>
5:13 pm - Wednesday April 20, 5938

ታማኝ ለአገሩ!  (ጌታቸው አበራ)

ታማኝ ለአገሩ!

ጌታቸው አበራ

እልል አለች ኢትዮጵያ – እጆቿን ዘርግታ ወደ ሰማይ፣

ታማኝ ውድ ልጇ ዘወትር – እንዳልተለያት ስታይ፤

 

“ይደልዎ!” አለ ሕዝቡ – ያገር-አድን ቅኔ እንደተዘረፈ ሁሉ

በ”አቋቋም”፣ በአካሄዱ… ተማርኮ በውብ ቃሉ፤

 

የጥበብ ነው ተፈጥሮው – ውበት ማስተዋልን የታደለ፣

ላገር፣ ለሕዝብ በእምነት አድሮ፣ – የፍቅር ህያው ሃውልት የተከለ፤

 

ታማኝ ለሙያው ክህሎት – የመድረኩ ጸዳል አብሪ፣

በፈጠራው መንፈስ-አዳሽ – አገር ወዳድ ወገን አኩሪ፤

 

“የትዕይንተ-ጥበባት” ሞተር – የብሔራዊ ትያትር ዋልታ፣

የመድረኩ መሪ ተዋናይ – ጥበብ ለተጠማ አለኝታ፤

በ”ዘመነ-ውጥረት” ማግስት – የታዳሚው ሳቅ አፍላቂ፣

ኢትዮጵያዊው ብላቴና – ትኩስ ህይወት ተፍለቅላቂ፤

 

ባለቅባት፣ ባለጸጋ – ተሰጥዖ ለኪነት፣

በቀልዳ-ቀልድ እያዋዛ – አሳላፊ ክቡር እውነት፤

ከ”ፋሲሊደስ”..እስከ “ሕዝብ ለሕዝብ”…

ከ”ሮሃ” እስከ “ደመራ”፣

አንጸባራቂ ኮከብ – በኪነቱ አለም ጎራ።

 

 …የሕዝብን ድምጽ አስተጋቢ – ሃሳቡን ተንታኝ ያለፍርሃት፣

  ከ”ስቴድዮም” እስከ “ዲሲ” – ከ”ሲ-ኤን-ኤን” እስከ “ኢሳት”፤

ከ”አኬልዳማ” እስከ “ፌዝ-ራሊዝም” – በመልሶ ማጥቃት ዝና፣

በመረጃ እሚያጋልጥ – የ”ኢቲቪ”ን ጉድ ገመና፤

ከአሜሪካ እስከ አውሮፓ – ከኦሺያንያ እስከ አፍሪካ፣

እንደ አበባ ጽጌረዳ – በየዕለቱ እሚፈካ።

   የመጥምቁ አምሳያ – ጭው ባለው በረሃ ጯኺ፣

   ከድቅድቅ ጨለማ ውስጥ አሻግሮ – መጪዋን የብርሃን ቀን ጠቋሚ።

    “እኔ በቃላት አጠምቃችኋለሁ፤ በመንፈስ የሚያጠምቃችሁ ከኋላ ይመጣል፤”

   እያለ ለኢትዮጵያውያን – እሚረጭ ያንድነት ፈዋሽ ጸበል።

 

ከባድ ሸክም ያረፈበት – የትውልዱ መሪ አውራ፣

ብሩህ ተስፋን ሰንቆ – ለጨለመበት እሚያበራ፤

የጭንቅ አጋር.. ያገር ሲሳይ – የወገኑ ባላደራ፤

 

የአንድነት ምልክቱን – ሃገራዊ ክቡር ዓርማ፣

ሕዝብ በእምነት ያስረከበው – የኢትዮጵያን ሰንደቅ ዓላማ፤

ምንኛ መታደል ነው – ለሕዝብ አደራ መታጨት፣

ለካስ ይሄ ነው ምስጢሩ – “ስምን መልዓክ ያወጣዋል” ማለት፤

ወድቃ-ደቃ እንደማትቀር ስታውቅ – እልል አለች አገሬ፣

አዕላፋት አፍርቶ – ተስፋ ሲሆናት ‘አጅሬ’!

የአንድነት ዋስ ጠበቃ – ሁሉን-አቀፍ አንጋቹ፣

በኪነቱ፣ በ”አክቲቪስቱ” – ለሰው ልጅ መብት ተሟጋቹ፤

 

“የሕዝብ ጆሮ፣ የሕዝብ ዐይን” ነጻ ሚዲያ ለመገንባት፣

ቤት፣ ንብረቱን፣ ልጆች፣ ሚስቱን፣ – ትቶ ባለም ሲንከራተት፣

ላንድ ራሱ ያለው ጸጋ – የሚያፈራው ዕንቁ ዋጋ፣

ጭብጨባ ነው ወረቱ – አጀብ-ድምቀት ንብረቱ፣

ህሊናዊ እርካታ ነው – ሰላም እንቅልፍ መተኛቱ፤

(ለኛም አዟል ይቺን “ኪኒን” – በዘወትር ስብከቱ)።

 

ባለም ዙሪያ በሕዝብ ነግሦ፣ በሄደበት ፍቅር አፍሶ፣

የትውልዱ ዕሴት ዋጋ – እማይገኝ በፍለጋ፤

 

እልል አለች ኢትዮጵያ—እጆቿን ዘርግታ ወደ ሰማይ፣

ታማኝ ውድ ልጇ ዘወትር— እንዳልተለያት ስታይ፤

 

“ይደልዎ!” አለ ሕዝቡ— ያገር-አድን ቅኔ እንደተዘረፈ ሁሉ፣

በ”አቋቋም”፣ በአካሄዱ… ተማርኮ በውብ ቃሉ፤

 

የጥበብ ነው ተፈጥሮው— ውበት ማስተዋልን የታደለ፣

ላገር፣ ለሕዝብ በእምነት አድሮ – የፍቅር ህያው ሃውልት የተከለ!

 ጌታቸው አበራ

የካቲት 2005 ዓ/ም

(ፌብሯሪ 2013)

የሕዝብ “ሃብት” ለሆንውና ለተወዳጁ ታማኝ በየነ መታሰቢያነት ከዛሬ አምስት ዓመታት በፊት ፣ የጫርኳትን ይህቺን ግጥም ዳግም ለንባብ ለማብቃት የወደድኩት፤ ታማኝን፣ ቤተሰቡን፣ መላውን አገር-ወዳድ ደጋፊዎቹንና አክባሪዎቹን እንኳን ደስ ያላችሁ፣ እንኳንም ለዚህች ዕለት አበቃን ለማለት ነው።

Filed in: Amharic