>

ለውጥ መቼ መጣ!? (አንዱአለም ቦኪቶ)

ለውጥ መቼ መጣ!?
አንዱአለም ቦኪቶ
በርግጥም በብዙ ጉዳዮች ላይ ለውጥ መምጣቱ ባይካድም በአንዳንድ ጉዳዮች ላይ ግን “ለውጥ መቼ መጣ?” የሚያስብሉ ነገሮችን እያየን ነው፡፡
አንዳንዴ የመንግስት ብቻ ሳይሆን የእኛም ነገር ግርም ይለኛል፡፡በተለይ የእኔ ነገር ግርም ይለኛል፡፡ምንም እንኳን በሁሉም ነገር ላይ የመናገር ግዴታ ባይኖርብኝም ስለ ኢንሳው ቢኒያም ተወልደ እስከ አሁን ያልኩት ነገር አለመኖሩ እየገረመኝ ነው፡፡ የሆነ ሆኖ ዛሬ እንኳን የዚህን ልጅ ጉዳይ በሀገራችን ካለው የፍትህ እና ፖለቲካ ስርአት አንጻር እንወያይበት እስቲ ….
እንግዲህ እንደማንኛውም ተራ ዜጋ ስለ ቢኒያም የማውቀው በሙስና ወንጀል ተጠርጥሮ በፖሊስ ከተያዘ በኋላ ፍርድቤት እየተመላለሰ ያለ ግለሰብ እንደሆነ ነው፡፡ “ሙስናውን ፈጽሟል አልፈጸም? “ይሄን ለጊዜው እሱና ፈጣሪ ብቻ የሚያውቁት ጉዳይ ሲሆን ኋላ ላይ ፍርድቤትም ስለጉዳዩ “ፈጣሪ እና ቢኒያም ብቻ የሚያውቁትን” ሲያውቅ ልጁ ወይ” ነጻ “ይባላል ወይ ወደ ሸቤ ይዶላል፡፡እስከዛው ግን እንደማንኛውም ሰው ንጹህ እንደሆነ የመገመት መብት አለው፡፡…
“ታዲያ እንዴት እስከዛው ይታሰራል?!” ለሚለው የፍትህ ስርአታችን ለሁሉም ተጠርጣሪዎች ያዘጋጀው “ዋስትና” የሚባል መላ አለ፡፡የተጠረጠረው ሰው ምናልባት እንኳን ነጻ ሆኖ ቢገኝ በመሃል ያሰርነው እንዳይቆጨን የተዘጋጀች ምርጥ አለምአቀፍ መላ ነች፡፡ችግሩ በሙስና የተከሰሰ ሰው (ሁሉም ባይሆንም) ዋስትና የመከልከል እድሉ ከአዋጁ አንጻር ሰፊ መሆኑ ነው፡፡
ለዚህ ደግሞ የህጋችንን ክፍተት አይተው አዲሱ ጠሚያችን ያበጁት እና ቃል የገቡልን መላ አለ ….
ደስ አይልም!?
ምን መሰላችሁ ..?!
ጠሚው የተመረጡ ሰሞን በዛ ማር ማር በሚል አፋቸው ..”የኢትዮጲያ ህዝብ ሆይ ከዛሬ ወዲህ ማንንም ሳናጣራ አናስርም!…አስረን ምርመራ የምናደርግበት ዘመን አክትሟል”ብለውን ነበር፡፡
ጎሽ! ፖሊስ እንደድሮው ሰውን ከያዘ በኋላ “ቆይ ይሄ ሰውዬ ምን ነበር ያደረገው ?!” ብሎ….”አንተ! እስቲ አስታውሰን !ለምን ነበር የያዝንህ !?”እያለ የሚገርፍበት ዘመን አብቅቷል ብለን ጨፍረንም ነበር፡፡
አሁን እንደምናየው ግን “ዘ ሴም ኦልድ ስቶሪ” እየቀጠለ ነው፡፡ ….ታሳሪና አሳሪ የቋንቋ ለውጥ አድርገው ቦታ ተለዋወጡ እንጂ በዚህ ረገድ ምንም የታየ ለውጥ የለም፡፡…
ድሮም ታሳሪን ደግፈው “እከሌ የታሰረው በፖለቲካ ልዩነቱ እንጂ ሰርቆ አይደለም !”የሚሉ ግሩፖች ፍርድቤት ግቢ ውስጥ ይታዩ ነበር…. አሁንም እንደዛው …ያሁኑ ልዩኑቱ ግሩፑ በትግርኛ ማውራቱ ብቻ ነው፡፡
ለጠሚው ግዜ ይሰጣቸው! ግዜ ይሰጣቸው! …አይ ኖው ግዜ እንደሚያስፈልጋቸው!ይሄን ሳላውቅ አይደለም የማወራው !  ቢያንስ ቢያንስ ግን አጣርቶ ለማሰር ወይም ሳያጣሩ ላለማሰር የቁርጠኝነት ጉዳይ እንጂ ምንም ቅደመ ሁኔታ የሚያስፈልገው ነገር እንዳልሆነ መረዳት አለብን፡፡ ከታሳሪዎች ጀርባ እኮ አንድም ቀን አባታቸውን ሳያዩ ለማደር የማይፈልጉ ልጆች፡ሚስት ፡እናት አባት …ወዘተ አሉ፡፡በዛ ላይ ስንትና ስንት ሰዎች መጨረሻ ላይ የታሰሩት “በስህተት” እንደሆነ ስናይ ነው የከረምነው እኮ ወገን!..
ከዘረኝነት እና ከጭፍንነት…ከስሜታዊ እና መንጋዊ ደምዳሚነት ወጥተን ህሊናችን እና እውቀታችን እስከፈቀደልን ድረስ ወደ ውስጣችን ዘልቀን ጉዳዩን ብናየው ደስ ይለኛል፡፡…በዚህ ጉዳይ ላይ ግን አእምሮአችን “አሻፈረኝ አልሰማህም/አልሰማሽም!” ካለን ስለራሳችን ያለን ግምት የተዛባ.. እንደውም ባልጩት እራስ ዘረኞች መሆናችንን ተቀብለን መቀጠል ነው..ሎል..እኔ በበኩሌ ሂሴን ውጫለሁ፡፡
ሌላ የፍትህ ስርአቱ አለቃ እንጂ አቋም እንዳልቀየረ የሚያጠራጥረኝ …ደግሞ የኢንጂነሩ ጉዳይ ነው፡፡እስቲ ኢንጂነር ስመኘው ከተገደሉ ስንት ቀን ሆናቸው!? እስከ አሁን እኮ የተነገረን ምንም ነገር የለም … በዚስ ረገድ የመጣው ለውጥ ምንድነው እስቲ..!? መልሱልኛ!
ጠሚ ሆይ ቀስ በቀስ በተለይ በአንዳንድ ጉዳዮች ወደ ቀደመው ስርአት እንዳንመለስ …እየፈራን ነው፡፡በተለይ እጅግ አንገብጋቢ በሆነው የፍትህ ስርአት! …..ተከሳሹ/ተጠርጣሪው ማንም ይሁን ማን ፍትህን በተመለከተ ቁርጠኛ አቋም ይወስዱ ዘንድ እለምኖታለሁ፡፡..ከእርሶ በፊት የነበሩ መሪዎች በሙሉ በዚህ ጉዳይ ሁሉም ተለምነው መስሚያቸው ጥጥ ነበር፡፡
የፍትህ አስተዳደሩን እጅግ በጣም ያስቡበት! የፍትህ አስተዳደሩን ያስቡበት!…የፍትህ አስተዳደሩ ነጻ መሆኑ ለእኔም ለእርሶም ለህዝቡም ወሳኝ ጉዳይ ነው…ማንኛችን እንደምናልፍበት ዛሬ ላይ የሚያውቀው ኃያሉ ፈጣሪ ብቻ ነው! ….የእኛ(የእርሶም ጭምር) ድርሻ በጊዜ ነጻና ፍትሃዊ መስመር ዘርግቶ መጠበቅ ብቻ ነው፡፡
(እላይ ስለጻፍኩት ጉዳይ በቁም ነገር እንደትወያዩበት እፈልጋለሁ …ኤንድ ፊል ፍሪ ቱ ሴይ ኤኒ ቲንግ….ተካዎችም ብትሆኑ ሎል፡፡ …ጠቅላያችንም ትችት እና ጥቆማ እንጂ ጭብጨባ እንደማይረባቸው ተናግረዋል…ቢሆንም በእኔ ፔጅ ላይ ለዛሬ ለጠቅላዩ ካለ ጭፍን ፍቅር የተነሳ ከሚሰጥ የደንቆሮና መሃይም አስተያየት ጀምሮ የፍትህ ስርአቱን በመረዳት የሚሰጡ ማናቸውንም የሰሉ ትችቶችንም ጭምር ለማስተናገድ ዝግጁ ነኝ፡፡)
ሰሞኑን እረፍት ላይ ስለሆንኩ በተደጋጋሚ እከሰታለሁ፡፡ብዙ ጉዳዮች ላይ እንወያያለን፡፡
እስከዛው  ይመቻችሁ
Filed in: Amharic