>

አጼው እና ዶክተሩ …..ለባለራእዮች የማትመቸ አገር!!! (አንዱአለም ቦኪቶ)

አጼው እና ዶክተሩ …..ለባለራእዮች የማትመቸ አገር!!!
በለዘብተኛ  ቋ.ተ አንዲ ማኛ
– አንዱአለም ቦኪቶ
እነ ደጃች ተድላ ጓሉ በነ አብዲ ኢሌ ተተክተዋል…እነ ዋግ ሹም ጎበዜ በነ አህመድ ናስር ተቀይረዋል..እነ ብሩ ሃይሉ በእነ ሽፈራው ሽጉጤ እነ ልጅ ጋረድ በነ ሲራጅ ፈጌሳና ደሴ ዳልኬ እነ ደጃች ንጉሴ በእነ አባይ ጸሃዬ ቢቀየሩም  አሁንም በተቃራራቢ የታሪክ ሽክርክሪት ውስጥ መሆናችን አይካድም!
 
በዚያን ዘመንም አገሪቷ በጎጥ የተከፋፈለች ነበረች፡፡መሳፍንቱ ሁላ በየጎራው የራሱን አስተዳደር መስርቶ አገር በሺ ብጥስጣሽ  መንግስታት ተካፋፍላ በታሪክ እስከ የመን ድረስ ግዛት እንደነበራት የተነገረላት ታላቋ ኢትዮጲያ አይሆኑ ሆና ባለችበት ወቅት” ካሳ” የሚባል ከቆመበት መሬት የትና የት አሻግሮ ማየት የሚችል ባለ ታላቅ ራእይ  ደቦል አንበሳ ቋራ ላይ ተነሳ፡፡…..
ከመቶ ሰባ ምናምን አመታት በኋላ ኢትዮጲያ ዳግም እንደዘመነ መሳፍንት ዘመን በጎጥ ተከፋፍላ የመበጣጠስ  አደጋ ውስጥ ወደቀች፡፡ፈጣሪም የቃልኪዳኗን ሀገር ፈጽሞ አልረሳትም ነበረና አብይ አህመድ የሚባል ገራም እና ባለ ትልቅ ራእይ ከጅማ አስነሳ፡፡…..
ካሳም ሆነ አብይ ማንም ሳይገምታቸው ራእያቸውን በሆዳቸው ይዘው የፊተኛው በፋሲል ቤተመንግስት የኋላኛው በሚኒሊክ ቤተመንግስት ሰተት ብለው ገቡ፡፡
ካሳም “ቴዎድሮስ” የሚለው ስም ኢትዮጲያን የሚታደግ የንጉስ ስም ለመሆኑ ትንቢት ነበረውና ዳግማዊ አጼ ቴዎድሮስ ተብሎ በኢትዮጲያ ምድር ነገሰ፡፡ ነገር ግን ገና ካሳ ከነገሰበት ቀን  ጀምሮ ጥቅማቸው የተነካባቸው መሳፍንቶች በየቦታው ማመጽ ቀጠሉ፡፡….በሰሜን  የትግራዩ ደጃች ውቤ ዘመድ የነበረው ደጃዝማች ንጉሴ ፡ በጎጃም ደጃች ተድላ ጓሉ..እነ ብሩ ሃይሉ…የደጃች ክንፉ ልጅ ..ልጅ ጋረድ የሸዋው የልኡል ሳህለስላሴ አመጽ ዳግማዊ አጼ ቴዎድሮስን በዘመቻና እና በጦርነት ባክኖ እና ተዋክቦ እንዲቀር አደረጉት፡፡ አንዱን አመጽ አብርዶ ከብዙ ድካም በኋላ ከመናገሻው ሲደርስ ሌላኛው አመጽ ፈንድቶ ይጠብቀው ነበር..….ያንዱን እሳት  ሲያበርድ ሌላኛው ይለኮሳል…ግና ምንም እንኳን እጅግ ፈታኝ ቢሆንም ቴዲ የኢትዮጲያን አንድነት በሰይፍ ሃይል አምጥቶላት እንደነበር ሁሉም ይስማማል፡፡..
አብይ ስልጣን ከያዘ በኋላ በተመሳሳይ ሁኔታ በየቦታው አመጽ ይበረታበት ይዟል….ሁኔታው የተለያየ ቢመስልም በይዘት ግን ያው ነው ፡፡እነ ደጃች ተድላ ጓሉ በነ አብዲ ኢሌ ተተክተዋል…እነ ዋግ ሹም ጎበዜ በነ አህመድ ናስር ተቀይረዋል..እነ ብሩ ሃይሉ በእነ ሽፈራው ሽጉጤ እነ ልጅ ጋረድ በነ ሲራጅ ፈጌሳና ደሴ ዳልኬ እነ ደጃች ንጉሴ በእነ አባይ ጸሃዬ ቢቀየሩም  አሁንም በተቃራራቢ የታሪክ ሽክርክሪት ውስጥ መሆናችን አይካድም፡፡ ….በቴክኖሎጂ እርዳታ ሰውየው ከቦታ ወደቦታ እየዞረ ወደ ዋና ከተማው ስለሚመለስ እንጂ በአገሪቷ ሆነ ተብሎ በተቀነባበሩ አመጾች እዚህም እዛም የሚሎኮሱ እሳቶችን ለማጥፋት እንደባጀ ነው፡፡
የሚገርመው ደግሞ ቴዎድሮስ ስልጣን ከያዘ በኋላ ባሉት የመጀመሪያ ሁለት አመታት ማለትም ከ1855-1857 (እ.ኤ.አ).. ብቻ 17 ግዜ የግድያ ሙከራ የተደረገበት ሲሆን  አብይ ስልጣን ከያዘ ገና በ3 ወሩ የመጀመሪያው የግድያ ሙከራ በአደባባይ  ተፈጽሞበታል….የወደፊቱን  ባናውቅም እቺ አገር ባለራእይ አይበርክትልሽ ተብላ የተረገመች ይመስላል፡፡
ግርም የሚለኝ  ብርሃኑ ዘሪሁን በጻፈው “የታንጉት ሚስጥር” በሚለው ታሪክ ቀመስ ልብወለድ ላይ  አጼ ቴዎድሮስ ለታንጉት እንዲህ ሲሏት ይነበባል…”አሁን ደግሞ  እኛ የታላቋን ኢትዮጲያ ዝናዋን ለመመለስ ስንፈልግ ጠላት ሊያደክማት የሚሰራውን ይሰራል…ይኸ ተንኮል ያልገባው የእኛ ሰውም ተነሱ ጋር አብሮ ሊያፈርስ ይቆፍራታል፡፡ ሌላው ደግ ይኸው የዘመነ መሳፍንት ጨምላቃ  የቀድሞ ኑሮውን እንደ ትልቅ ነገር ቆጥሮት ያ ለምን ተነካብኝ ብሎ በዚህም በዚያም ይዶልታል…”…(ገጽ 67)
አብይ በተመሳሳይ ይህንን ነገር በተደጋጋሚ ሲናገር ይደመጣል…….”ስልጣን ይዞ የቆየው ክፍል አገሪቷን ከፍላ የማትጨርሰው የብድር ማጥ ውሥጥ ዘፍቋት ሲያበቃ ጭራሽ በፍቅር የያዝከውን እንደያዝክ  ተደመር ቢባል የሌብነቱን የኑሮ ዘመን እንደኑሮ  ቆጥሮ ተደመር ቢባል አሻፈረኝ ብሎ በዚህም በዚያም ይዶልታል…”
 ቃል በቃል ባይሆንም አጼ ቴዎድሮስ “አጋሰስ” የሚሏቸውን አብይ ደግሞ “የቀን ጅቦች” በማለት የሚጠሯቸውን የቀደምት ባለስልጣናት በተመሳሳይ ሃሳብ ያማርሯቸዋል፡፡  
 አብይም ሆነ ሰፊው ህዝብ ጠላቶቹ የደገሱለትን ሳያውቅ በመስቀል አደባባይ ተገኝቷል…እኔም በዚህ የህዝብ የፍቅርና የአንድነት ማእበል ውስጠ ሆኜ  …..በአእምሮዬ ውስጥ በለሆሳስ ሳዳምጥ የነበረው ይሄንን የቴዲን ግዜ አይሽሬ ዘፈን ነበር .
“….ዝግባ ሚያሳክለን አንድ ፍቅር አጥተን …    ዝግባ ሚያሳክለን አንድነትን አጥተን
    ከፊት የነበርነው ከሰው ኋላ ቀርተን ……..     አናሳዝንም ወይ ……እርርር………..
    ጎንደርና ጎጃም ወሎና ትግራይ …          ኦሮሞና ተጉለት  ሆነን አንድ ላይ”
     ጉራጌና ሀረር …..ዶርዜ ወላይታ …  ቤኒሻንጉል ሶማሌ አፋር አሳይታ
    ግመሌን ላጠጣት እንደ አፋር ተጉዤ…… ግመሌ ላጠጣት ቀይባህር ተጉዤ
     አንድ ገመድ አጣሁ……. ልመልሳት ይዤ
    የአንዲት እናት ልጆች መሆናችን አውቀን…. ጎሳና ሃይማኖት ሳይነጣጥለን
     ምን ይሳነን ነበር ብንተባበር…..እርርር
እያልኩ በአይኔ እምባ ሞልቶ ሊፈስ ጫፍ በደረሰበት ሰአት መንፈሴ ሙሉ በሙሉ ፍቅር በተሞላበት ቅጽበት የፍንዳታ ድምጽ ተሰማ፡፡ ከመቅጽበት ነገሮች እንዳልሆኑ መሆን ጀመሩ…….ፍንዳታው በተሰማ የመጀመሪያው ቅጽበት ነገሩን ርችት እና መሰል ከክፋት ነጻ ከሆኑ የፍንዳታ ድምጾች ጋር ባያይዘውም …ወዲያው ነበር ከመድረኩ አካባቢ ከማየው ግርግር ምን እየተካሄደ እንደነበር የገባኝ…..ይህ ይመጣል ብሎ ያልጠረጠረው አብይ ብድግ ብሎ ቆመ፡፡ድምጹን ወደሰማበት አቅጣጫ ዞሮ ሲቆም አየሁት….የተቃጣበት ነገር ይገባዋል…
እህህህ  ና…ና…..  ሲል …ና…..ና
ደርሶ ላያስጥለው ለምዬ ባይደርስለትም….
ተዋከበና………. ና…..ና….. ተዋከበና
ወዲህ ዞር ቢል ሰው የለምና
ወዲያ  ዞር  ቢል ለማ የለምና……………..ይቀጥላል፡፡
(መታሰቢያነቱ  ትንናት በሙሉ ጤንነት ወደ አገራቸው ለተመለሱት የተከበሩ አቦ ለማ መገርሳ ይሁንልኝ፡፡)
Filed in: Amharic