>

የኢንጅነር ስመኝ አሟሟት በማን?፣ ለምን? የሚለው ጥያቄ እንደተለመደው ምላሽ አያገኘም!?! (ቬሮኒካ መላኩ)

የኢንጅነር ስመኝ አሟሟት በማን?፣ ለምን? የሚለው ጥያቄ እንደተለመደው ምላሽ አያገኘም!?!
ቬሮኒካ መላኩ
ይች አለም ብዙ ግፍ ሰርታለች ክርስቶስን በመስቀል አንጠልጥላለች ። ሶቅራጥስን በሄምሎክ ገድላለች ።እስጢፋኖስን በድንጋይ ወግራ ገድላለች ።ማርቲን ሉተርን በጥይት ደብድባ ገድላለች ።
ይች የእኛ  አገርም  በአቅሟ ብዙ ግፍ ሰርታለች።
* ቴዎድሮስ ለራሷ ሲዋትት ኖሮ  በመጨረሻ  ከቀትር  በኋላ  ጀምበር ሳትጠልቅ ሂይወቱን ሲሰዋላት ተመልክታለች።
* ልጅ ኢያሱ ማን እንደገደለውና አፅመ ስጋው  የየትኛውን አካባቢ አፈር እንደቀመሰና  እንደ አረፈ ዛሬም አላውቅም ብላናለች።
* ስንት ውለታ የዋሉላትንና የደከሙላትን  አፄ ሀይለስላሴን በግፍ በትራስ ታፍነው ሽንት ቤት ስር ሲቀበሩ ተመልክታለች። ባንዳ ሾማ በላይ ዘለቀን ገመድ ላይ አንጠልጥላለች ፣ መንግስቱ ንዋይ፣ ገርማሜ ንዋይ፣ ተፈሪ በንቲ፣ አጥናፉ አባተ ፣ ስልሳዎቹ መኳንንቶች እንቁ የሀገር ሀብቶች እኒህን እና በርካታ ስም አልባ ዜጎችና በጅምላ እና በተናጥል በየስርቻው ቀብራለች።
በአሉ ግርማ እንደ ነቢዩ ሙሴ መቃብሩን አላውቅም ብላለች ። ባለፉት 25 አመታት በ10 ሺዎ የሚቆጠሩ ዜጎች የት እንዳሉ አይታወቅም ።
ዛሬም የዚች አገር መንግስት ከታሪክ መማር አቅቶት በአደባባይ ብዙ ዉለታ የዋለላትን የኢንጅነር ስመኘውን በቀለ ገዳይ ምስጢሩ እንዳይወጣ እየተጋች ትገኛለች።
  ፈረንጆች ” እንደ አሪስቶትል  ለመናገር ላይቸግር ይችላል ፣ እንደ ሶቅራጥስ ግን የተናገሩትን ሆኖ መገኘት እጅግ ከባድ ነው ።” ይላሉ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር  አቢይ አህመድ  ባለፈው ፓርላማ ላይ ” ከእንገድህ  በኋላ ከህዝብ የምንደብቀው ነገር የለም !” ባሉን መሰረት አሁንም የኢንጅነሩን ገዳይ ለኢትዮጵያ ህዝብ እንድያሳውቁን እየጠበቅን ነው።
እርግጥ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ቃል የገቡልንን  እንደ ጴጥሮስ ዶሮ ሳይጮህ  ይከዱናል ብዬ አላምንም እንደ አሪስቶትል መናገር ብቻ ሳይሆን እንደ ሶቅራጥስ የተናገሩትን ሆነው ይገኛሉ ብዬ አምናለሁ።
ዛሬም የኢንጅነር ስመኘው  በቀለ ነፍስ በትዝብት እየተመለከተችን ነው ። ካለበለዚያ እንደ አካኪያ አካኬቪች ነፍስ  ግፏን ቆጥራ  በጎስት እየመጣች ለመረበሽ   የቤተመንግስት አጥርና ጥበቃ ያግዳታል ማለት ዘበት ነው  ። ከህግ ፍርድ ማምለጥ ቢቻልም ከዘመንና ከታሪክ ፍርድ ግን ማምለጥ አይቻልም።
Filed in: Amharic