>

የሙስሊሙ ስጋት፣ ተስፋ  እና ምላሽ የሚሹ ሃሳቦች!!! (አህመዲን ጀበል)

የሙስሊሙ ስጋት፣ ተስፋ  እና ምላሽ የሚሹ ሃሳቦች!!!
አህመዲን ጀበል
አዲሱ አመራር የሙስሊሙን ጥያቄ በተመለከተ በቅርቡ ምላሽ ይሰጥበታል የሚል እምነቴ ያነሰ ነው፡፡ ተስፋችን ግን የጨለማ አይደለም፡፡ ሙስሊሙ እንደሚፈልገው ቶሎ ምላሹን ከሰጠ አልሃምዱሊላህ፡፡ አሁን ካለው ሁኔታ አንፃር ግን የሙስሊሙን የመብት ጥያቄ በተመለከተ አዲሱ አመራር ከበፊቱ የተለየ እሳቤ እስካሁን አልያዘም፡፡ ሁሉም ከዚህ በፊት በነበረው ሂደት እንደቀጠለ ነው፡፡
 በመላው ሃገሪቱ እና በመላው አለም የሚገኙ ኢትዬጲያውያን ሲያነሷቸው የነበሩ ቅሬታዎች ደረጃ በደረጃ እየተፈታ ወደ እርቅ እና ሰላም እየተኬደ ነው፡፡ የሙስሊሙ የመብት ጥያቄ ግን እስካሁን ችላ ተብሏል፡፡ይህ ችላ የተባለበት ምክንያት ሁለት አይነት እንድምታዎች እንዳሉት ይሰማኛል፡፡
በጥሩ ጎኖ ሲታይ ሌሎች ሁሉንም ወገኖች የሚመለከቱ ጉዳዬች አፋጣኝ ምላሽ እንዲሰጣቸው በማድረግ የማረጋጋት ስራ ከተሰራ ቡኋላ አንዱን ወገን ወደሚመለከቱ ጉዳዬች በመሄድ በጋራ በመመካከር ምላሽ የመስጠት ሂደት ታስቦ ይሆናል የሚል ነው፡፡
 ሁለተኛው እይታ ደግሞ ከስጋት ጋር የሚያያዝ ነው፡፡ የሙስሊሙን የመብት ጥያቄ ቸል በማለት በሌሎች ጉዳዬች የሃገሪቱን ህዝብ ልቦና መግዛት ከተቻለ አዲሱ አመራር በሙስሊሙ ዙሪያ ከዚህ ቀደሙ የነበረውን አካሄድ ይዞ ቢቀጥል እና ተቃውሞ ቢቀብበትም እንኳን እንደበፊቱ  ሙስሊም ያልሆነውን ብቻ ሳይሆን  ሙስሊም የሆነውንም ወገን ድጋፍ ላያገኝ ይችላል በሚል ቀስ በቀስ የመሸርሸር እና የማዳፈን ስራም ታስቦ ሊሆን ይችላል፡፡
ሙስሊሙ መስቀለኛ መንገድ ላይ ይገኛል፡፡የዶ/ር አብይን የለውጥ እንቅስቃሴ ለመቀልበስ እያሴሩ የሚገኘው ሃይል ሙስሊሙን በመተንኮስ እና በማስቆጣት ወዳልተፈለገ ግጭት እንዲያመረ ለማድረግ አድብቶ እየጠበቀ ነው፡፡ በተለይ ሙስሊሙ በሚበዛባቸው ክልሎች ላይ በአክራሪነት ሽፋን ጥቃት በማድረስ የሃይማኖት ግጭት ለመፍጠር እየተንቀሳቀሱ ነው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ሙስሊሙ ማህበረሰብ ለጠየቀው ጥያቄ እስካሁን ምላሽ አለመሰጠቱ ቅሬታን እየፈጠረበት ነው፡፡ ይህ ቅሬታ  መቅረፍ ካልተቻለ የለውጡ አደናቃፊዎች ላቀዱት ወጥመድ ምቹ ሁኔታን እንዳይፈጥር ያሰጋል፡፡
የመብት ጥያቄውን ምላሽ በትዕግስ እንጠብቅ እንዳይባል አህባሽ መራሹ  ህገ ወጡ መጅሊስ ከጠ/ሚኒስተሩ “አይዟችሁ ከጎናችሁ ነኝ፣እናንተ ብቻ ተጠናከሩ” የሚል ማረጋገጫ ተሰጥቶናል እና ጠንክረን እንስራ የሚል መልዕክት ለአባሎቸው እያሰተላልፉ ይገኛሉ፡፡ ዶ/ር አብይ አህመድ ይህን ብሏል በሚል ከሙስሊሙ ማህበረሰብ ጋር  እሱን ለማጋጨት የታቀደች ሴራ ይሁን ወይንም ደግሞ ዶ/ር አብይ በትክክል ይህን ብሎ እንደሆነ የታወቀ ነገር የለም፡፡  ይህን ብሏቸውስ ከሆነ ቀጣይ ሙስሊሙ የሚገጥሙት ተግዳሮቶችን በምን መልኩ ሊያልፋቸው ይገባል?
ይህን በፍፁም ሊላቸው አይችልም ካልንስ  በትዕግስት እንጠብቀው ወይስ የሙስሊሙን የመብት ጥያቄ ችላ ማለቱ ከበፊቱ አመራር የተለየ አቋም ስሌለለው ነው የሚል ድምዳሜ በመያዝ  ተጠናክሮ ለመታገል ሙስሊሙ መንቀሳቀስ ይኖርበታል ??
ለውጡን ለማደናቀፍ እየታገለ የሚገኘው ቡድንስ ሙስሊሙን በመጠቀም ሃገሪቷን ለማተራመስ ያቀደውን ሴራ ሙስሊሙ እንዴት ሊያከሽፈው ይችላል??
እነዚህ ምላሽ የሚሹ ጉዳዬች ናቸው
Filed in: Amharic