>

ምኒልክ እና መኪና (ዳዊት ሰለሞን)

በአዲስ አበባ የመጀመሪያው መኪና የገባው ከዛሬ 110 ዐመት በፊት በዳግማዊ አጤ ምኒልክ ዘመነ መንግስት ነበር። ቤንትሌይ የሚባል እንግሊዛዊ ስለምኒልክ የስልጣኔ   እና ቴክኖሎጂ ፍላጎታቸው ይሰማ ነበር። ምኒልክ መኪና የሚባለውን እየሰሙ ለማየት እንደሚጓጉ አወቀ። እሱም መኪና ይዞ አዲስ አበባ ለመግባትና ለምኒልክ ለማሳየት ወሰነ። ይህን ለማሳካት ግን ለዚህ ረጅም እና አስቸጋሪ ጉዞ ጠንካራ መኪና እንደሚያስፈልግ አውቆ ለአንድ መኪና የሚሸጥ ኩባንያ ስራ አስኪያጅ ለሲድሌይ አጫወተውና መኪና መረጣ ጀመሩ። መኪናውን ካገኝ በኋላ ጎበዝ ሹፌር መረጣ ጀመረ። ለዚህም ዌልስ የሚባል ጓደኛው በአነዳዱ ስላስደሰተው አብሮት ወደ ኢትዮጽያ እንዲሄድ ጠየቀው። መኪናውን ይዘው ዌልስ እየነዳ ቤንቴሌይ ከጎን ቁጭ ብሎ ከኋላ ቡሊ የሚባል ወጣት ከኋላ ጭነው ጉዞ ጀመሩ።
መኪናውን እየነዱ እስከ ማርሴል ወደብ ተጓዙ። ለጠቅላላው ለጉዟቸው የተለያዪ ኩባንያዋች የነዳጅ የስንቅ የቅያሪ ጎማዋች ስፖንሰር አደረጉ ። ከማርሴል ወደብ በመርከብ 27 ቀን ተጉዘው ጂቡቲ ደረሱ።  መኪናዋ ለጂቡቲም አዲስ በመሆኗ የፈረንሳይ ባለሥልጣናት ወደ አትዮጵያ እንዳትገባ ከለከሉ። ከዚያም ወደ ዘይላ ሄዱ። በእንግሊዝ ሶማሊያ አርገው በመጨረሻም ከኢትዮጲያ ግዛት ዱአሌ ሲደርሱ የክብር አቀባበል ተደረገላቸው። ድሬዳዋ ሲደርሱ ብዙ ጥይት ለክብራቸው ተተኮሰ።  መኪናው በሰዐት 65 ኪሜ የመሄድ አቅም እና 18 የፈረስ ጉልበት ነበራት። ከረጅም አስቸጋሪ ጉዞ ኋላ አዲስ አበባ ዙርያ ሲደርሱ ለክብራቸዉ መድፍ ተተኮሰ ብዙ ህዝብ በግራና በቀኝ አጅቦ ጉዞ ወደ መሃል ከተማ ጉዞ ሆነ። በታህሳስ 21 ቀን 1900 እቴጌ ሆቴል አርፈው ትልቅ ግብር ቀረበላቸው። ምኒልክም አምጡና ልያት ብለው መልእክተኛ ላኩ። መኪናዋ ቆሽሻ ስለነበር ቤንትሌይ በቆንስሉ በኩል ለምኒልክ አጥቦ ለማቅረብ ጊዜ እንዲሰጠው ጠየቀ። የእንግሊዝ ቆንስሉ መኪናዋ ታጥባ ነገ ጠዋት በቤተመንግስቱ ለማምጣት ቀጠሮ ያዙ። በቀጠሮው መሰረት ወደ ግቢ ገብተው መኪናውን አቁመው ምኒልክን እጅ ለመንሳት ወደ አዳራሽ ገቡ።
ምኒልክ ከነቤንትሌይ ጋር ከተዋወቁ በኋላ መኪናውን ለማየት ወደ ውጭ ወጡ። በቤንትሌይ አስረጅነት ስለመኪናዋ አንድ ባንድ ተረዱ። መኳንንቱና ህዝቡ ምኒልክ ወደ መኪናው እንዳይጠጉ መክረዋቸው ስለነበር ምኒልክም ለእንግሊዙ ቆንስላ ‘ ይሄ ሁሉ ማስፈራራት እኔ አልቀበልም ምክኒያቱም እኔን አንድ ሰው ለመግደል ይሄን ሁሉ መንገድ አቋርጦ የሚመጣ ወንበዴ የለም አሉት። ምኒልክም የቤንትሌይን ትከሻ ተደግፈው ሰው መኪናዋ አፈናጥራ እንደምትወረውር ያወራል ነገር ግን ሹፌሩንስ ለምን አጥለውም ለምዷት ከሆነ እሳቸውም ለምደው መንዳት እንደሚፈልጉ ገለፁለት። ምኒልክ የመኪናውን የውስጥ አካል ሲያዩ ቆንስሉ ለቤንትሌይ በጆሮው ንጉሱን አሳምንህ መኪናው ላይ ካሳፈርክ ብሎ በ 5 ፓውንድ ተወራረደው። ቤንትሌይም ለምኒልክ መኪናውን እንዲሞክሯት ጠየቃቸው። ምኒልክም የቤንትሌይን ጥያቄ በደስታ ተቀብለው የመኪናውን ፍጥነት ለመለካት እንዲህ አሉት አየህ ገብያው ለኛ በበቅሎ 30 ደቂቃ ደርሶ መልስ ይፈጅብናል  አንተ ከዛ ለመድረስህ የሚሸጥ አትክልት ይዘህ ና አሉት ከኋላም ሁለት አበሾች አሳፍረው ዌልስ እየነዳ ቤንትሌይ ከጎን ቁጭ ብሎ በሰዐት 50 ኪሜ እየነዱ ገበያ ደርሰው ምኒልክ የጠየቁትን አትክልት ይዘው ተመለሱ። ምኒልክም ጥሩ ነው 6 ደቂቃ ፈጀባቹህ ግን መኳንንቶቼን ስላስደነገጣቹህ አዝኛለሁ አሉ፣ መኳንንቶቹ ደንግጠው ስለነበር በድጋፍ ነበር የወረዱት። ምኒልክም ምን አስፈራቹህ እኔ እየነዳሁ አሳይችኋለው አሏቸው። ምኒልክም በመኪናው ወጠው ታህሳስ 22 ቀን ተሳፈሩባት። ዌልስ እየነዳ ቤንትሌይና ሆለር ከኋላ ተቀምጠው መኪናዋ ጉዞ ጀመረች እግረኞችም ፈረሰኞችም አጅበው ጉዞ ጀመሩ። መኪናዋ ፍጥነት ስትጨምር አጃቢው ወደ ኋላ እየቀረ ሄደ። ምኒልክም የአጀቡን መቅረት አይተው ” የበለጠ ፈጠን እንድያረጋት ንገረው” አሉት። መኪናዋም ፈጠነች።ምኒልክም ድስ ብሏችው ይስቁ ጀመር። በማግስቱም ከቤንትሌይ ጋር ሆነው ትንሽ ከተንሸራሸሩ በኋላ መንዳት እንደሚፈልጉ ነገሩት። በምኒልክ ፍላጎት መሰረት ቤንትሌይ ማስተማር ጀመረ።  ቁልፍ መክፈት ሞተር ማስነሳት ፍሬን መያዝ ማርሽ መለወጥ ዘይት መቀየር በየተራ ተማሩ። ምኒልክም መኪና መንዳት ጀመሩ። የመንጃ ፈቃድ ለመቀበል የመጀመርያውን ፈተና የተፈተኑት ምኒልክ ናቸው። አጃቢና ፈረሰኛውን ወደ ፊት ቅደም ብለው አዘው። ለሁለት ሰዐት ያህል ነድተው ለምስክሮች ችሎታቸውን አሳዩ። ግሩም ሸፌር ወጣቸው። ሄል የተባለ ጸሃፊ ፐርፌክት ድራይቨር ብሏቸዋል።
Filed in: Amharic