>

በጓዳችን መፈታት ደስ ብሎናል፤ የሚጠብቀን ብዙ መሆኑን እናውቃለን!!!

አርበኞች ግንቦት 7
ዛሬ ግንቦት 21 ቀን 2010 ዓም ጓዳችንና መሪያችን አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ከእስር ቤት ወጥቷል። አቶ አንዳርጋቸው ሰኔ 16 ቀን 2006 ዓም በሰንዓ አውሮፕላን ጣቢያ በህገወጥ መንገድ ተይዞ ያለአንዳች የህግ አግባብ ለህወሓት አገዛዝ ተላልፎ ላለፉት አራት ዓመታት በስቃይ አሳልፏል።
አቶ አንዳርጋቸው ዛሬ ተፈቶ ከጉጉት ከሚጠብቀው ሕዝብና ቤተሰቦቹ ጋር ሲቀላቀል እንደተናገረው “ሰው እየሳቀ ለመብቱም ለሕዝቡም መሞት እንደሚችል አሳያችኋለሁ” ማለት የቻለ መሪ ነው።
ለአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ እና ለሁሉም የህሊና እስረኞች መፈታት የበርካታ ወገኖቻችን ሕይወት መስዋትነት ተከፍሏል፤ ብዙዎች ታስረዋል፤ ተደብድበዋል፤ ተሰደዋል ሰቆቃ ተፈጽሞባቸዋል። ትግላችን እሚፈለገው ግብ ላይ ለመድረስ ገና ብዙ መንገድ የሚቀረው ቢሆንም ዛሬ የደረስንበት ለመድረስ ዋጋ ተከፍሎበታል። በኢህአዴግ ውስጥ ያሉ የለውጥ ኃይሎች ለዚህ ድል ከፍተኛ አስተዋጽዖ ማድረጋቸውን እንገነዘባለን።
አርበኞች ግንቦት 7: የአንድነትና ዲሞክራሲ ንቅናቄ በጓዳችን አንዳርጋቸው ጽጌ ከእስር መፈታት የተሰማውን ከፍተኛ ደስታ ይገልፃል። ይህ እውን እንዲሆን ጥረት ላደረጉ ኢትዮጵያዊያንን ዜጎች እና የሰብዓዊ መብት ተከራካሪ ድርጅቶች እንዲሁም ከጎናችን ለቆሙ የውጭ አገር ዜጎችና ድርጅቶች ሁሉ ከፍተኛ ምስጋና ያቀርባል።
ደስታው የሁላችንም ነው፤ እንኳን ደስ ያለን !!!
ደስታችን የተሟላ የሚሆነው ግን ወገኖቻችን የሞቱለት፣ የታሰሩለት፣ የተሰደዱለትና የተሰቃዩበት ዓላማ ሲሳካ ነው። ዛሬም አቶ አበበ ካሴ፣ ሰይፉ አለሙ፣ ፍቅረማርያም አስማማው፣ ማስረሻ ሰጤ፣ መስፍን አበበ፣ አበበ ኡርጌሳ፣ ራቪድ ሳላ እና ሌሎች በርካታ ወገኖቻችን በእስር ላይ ይገኛሉ። ለእነዚህ ሁሉ ወገኖቻችን ነፃነት የምናደርገው ትግል አጠናክረን መቀጠል ግዴታችን ነው።
ለፍትህ፣ ለነፃነት፣ ለእኩልነትና ለዲሞክራሲ የምናደርገው ትግል ገና በጅማሮ ላይ ያለው ነው። ዛሬ በአገራችን ያየነው መልካም ጅማሮ የኢትዮጵያን ሕዝብ እውነተኛ የስልጣን ባለቤት ወደሚያደርግ መሠረታዊ ለውጥ እንዲያመራ ትግላችንን አጠናክረን መቀጠል ይኖርብናል።
ስለሆነም በጓዳችን አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ መፈታት ምክንያት ደስታችን ከፍተኛ ቢሆንም ከእንግዲህ የሚጠብቀን ትግል ከዚህ በፊት ከነበረው የበለጠ መስዋትነት ሊጠይቅ የሚችል መሆኑን በመገንዘብ ተዘጋጅተናል። እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ የሀገሩ ባለሙሉ መብት ዜጋ እስኪሆን ትግላችንን እንቀጥላለን።
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ !!!
አርበኞች ግንቦት 7
Filed in: Amharic