>

እስኪ የህሊና ፍርድ ስጡበት! (ጌታቸው ሽፈራው)

ሻለቃ ይላቅ አቸነፈ ታዋቂ የአርማጭሆ ሽማግሌ ነበሩ። በዚህ እድሜያቸው ማዕከላዊ ታስረዋል። ሽብር የሚሉት የዘመኑ ክስ ተጠቅሶባቸው ቂሊንጦ እያሉ በቂሊንጦ ቃጠሎ ተገድለዋል።
ሻለቃ ቂሊንጦ ዞን2  በታሰሩበት ወቅት በእስረኞች  ትልቅ ክብር የሚሰጣቸው ነበሩ። መካሪ! እንኳን እንደ ሻለቃ ያለው ቀርቶ የትኛውም በሽብር የተከሰሰ ሰው በእስር ቤት ትልቅ ክብር ይሰጠዋል። ሻለቃን ግን ወንድሞቻቸው፣ በተመሳሳይ ክስ የተከሰሱት ምክር የሚጠይቋቸው ልጆች እንደገደሏቸው ተደርጎ ክስ ቀረበ።
ዛሬ ሚያዝያ  30/2010 ዓም ፍርድ ቤቱ በሰጠው ብይን ደግሞ ሟችም ተከሳሽ ሆነዋል። በዶክተር ፍቅሩ ማሩ ላይ የመሰከረ አንድ ግለሰብ ቃል ሲነበብ  ሻለቃ ይላቅ አቸነፈ እንደመለመሉት ገለፀ። ዶ/ር  ፍቅሩ ማሩም ምስክሩን አግኝተው “ሻለቃ ይላቅ ጋር እየተገናኛችሁ አውሩ። ጀግኖች አባቶቻችን ጣልያንን እንደጣሉት ሁሉ እኛም ይህን መንግስት ታግለን መጣል አለብን” እንዳሉት ይገልፃል። ምስክሩ።
እንደ ምስክሩ ቃል ሻለቃ ይላቅ አቸነፈ ቃጠሎው እንዲካሄድ ሲያደራጁ የነበሩ ሰው ናቸው። ግን ሻለቃ ይላቅ በቃጠሎው ወቅት ተገደሉ። እነ ማስረሻ ሰጤ ደግሞ ሻለቃ ይላቅንም ገድላችኋል ተብለው ተከሰሱ።
እዩ እንግዲህ የዚህን ሀገር ጉድ!
~ሻለቃ ይላቅ ቃጠሎው እንዲካሄድ ዋና አደራጅ ነበሩ ተባለ
~ሻለቃ ይላቅ እሳቸው እንዲቃጠል ሲያደራጁበት ነበር በተባለው ቂሊንጦ ቃጠሎ ወቅት ተገደሉ። በቃጠሎው ሰበብ የተከሰሱት ደግሞ ከሞቱ በኋላም ስማቸው በየ ፍርድ ቤት የሚነሳውን፣ ከእነሱ ጋር ዋና አደራጅ ነበሩ የተባሉትን ሻለቃን በመግደል ተጠየቁ። ሻለቃ ይላቅ በህይወት ቢኖሩ ይከሷቸው ነበር። በእርግጥ አሁንም ዋናው አደራጅ እንደነበሩ ተደርገው ስማቸው እየተነሳ ነው። የህወሓት ካድሬዎችን፣ ለመንግስት መረጃ የሚሰጡትን ገደሉ ተብለው የተከሰሱት 38ቱ ተከሳሾች ደግሞ በመንግስት ላይ አመፅ ሲያነሳሱ ነበር፣ ቂሊንጦን ለማቃጠል አደራጅተዋል የተባሉትን በመግደል ተጠይቀዋል!
(በቂሊንጦ ቃጠሎ ሰበብ የተከሰሱት ላይ ምስክር ሆነው ከቀረቡት መካከል አብዛኛዎቹ ለገዥዎቹ ስለ እስረኛው መረጃ የሚያቀብሉ፣ ቀሪዎቹ ደግሞ ተገርፈው በግድ የመሰከሩ መሆናቸውን በተደጋጋሚ በችሎት ተገልፆአል)
Filed in: Amharic