>
5:13 pm - Wednesday April 19, 9645

 “ሀገሬን ስትደፈር ከማያት ሀፍረቷን በደሜ አብሸላት መቆም እመርጣለሁ”  [አባ ኮስትር ደጃዝማች በላይ ዘለቀ]

በጉግሳ ይማም 
በላይ ዘለቀ የተወለደው ደቡብ ወሎ ጨቀታ ጅሩ ቀበሌ ጎጣ መንደር  ከአባቱ ከደጅ አዝማች ዘለቀ ላቀውና በእናቱ ቄንጦ   ከተባለ ዘረ ብዙ ሰዎች በአባቱም ሆነ በእናቱ የአርበኛ ዘር ሲሆን የወንድ አያቱ ላቀው ምርጥ ፈረሰኛ “ቆፍጣና ፈረስ ጋላቢ ላቅየ ባለጎራዴ” ብለው የሚፎክሩ የሚኒሊክ ጦረኛ ነበሩ፡፡ በላይ በትውልድ እድገቱም ጨቀታ ቀበሌ የገዛዝ አቦ ለገበር የተባለ ሰፊ እርስት ነበር፡፡አባቱ ሰው ሲገል ወደ ጎጃም መጣ፡፡
የበላይ አርበኝነት፡- 
በርሃ የገባው በ1928 ዓ/ም ወገኖችንና ዘመዶችን በመሰብሰብ ነበር፡፡ ከበረኞች ከፊሎቹ ሲስማሙ ግማሾች ተቃውሞውት ነበር፡፡የፈሩበት ምክንያትም ጣሊያንን ንጉስ ያልቻለውንን ዘመናዊ ትጥቅ ከያዘ ወራሪ ጋር እንዴት አድርገን እንዋጋለን በማለት ሲሆን እርሱም የፈራ ቅር እኔ ግን “ሀገሬን ስትደፈር ከማያት ሀፍረቷን በደሜ አብሸላት መቆም እመርጣለሁ” ካለ በኋላ ቆራጥ ተከተል ብሎ ከወዳጅ ዘመዶቹ ጋር ለአርበኝነት ለመጀመሪያ ጊዜ ተነሳ፡፡ በዚህም ታላቅ የጦር መሪና ስልት ነዳፊ የተዋጣለት ተዋጊና አዋጊ  መሆኑን አስመሰከረ፡፡ በላይ ዘለቀ መልዕከ ብርሃን ገብረ ጊወርጊስ የኢትዮጲያ ደም መላሽ የሚል በራሱ ስም ማህተም አስቀርፆ አርበኞችን ማሰባሰብ ጀመረ፡፡
የለምጨን ጦርነት፡-
የእነ በላይ ጦርነት ለመጀመሪያ ጊዜ ግንቦት 1928 ዓ/ም በጎጃም ምድር በመጣው የጠላት ሃይል ላይ ለምጨን በደፈጣ ውጊያ ተጀመረ፡፡በዚህ ውጊያም በላይ አንድ የጣሊያን ወታደር በመግደልና እና ሌሎችን አቆሰላቸው፡፡ሌሎች በርካታ ቁጥር ያላቸው ባንዳዎችን በቁጥጥር ስር አዋላቸው፡፡ይህም የነበላይ የመጀመሪያው ውጊያና ድል ነበር፡፡
የአባራ ጊወርጊስ፡-
ሰኔ 19/ 1928 ዓ/ም ከለምጨን ውጊያ ያፈገፈገው የጠላት ሃይል ሰማ ነጎ የተባለው ባንዳ ተጨማሪ ጦርና መሳሪያ ይሰጠኝ እንጅ እኔ በላይ ዘለቀ ሲሆን ከነነፍሱ ይዤ ቢቀር አንገቱን ቆርጨ ለ3 ቀን ባልበለጠ ውስጥ አመጠዋለሁ በማለት የጣሊያነን ጦር አዛዝ በመጠየቅ በነበላይ ላይ ዘመተ፡፡
የአባራ ጊወርጊስ ነዋሪዎችንም በላይ ዘለቀን ሸሽጋችሁ እያበላችሁና እያጠጣችሁ አጎለበታችሁት ስለዚህ የተሰቀለበትን ተናገሩ በማለት አሰቃያቸው፡፡በወቅቱ በላይ ዘለቀ ከለምጨን ወደ አባ በመሄድ ላይ  የህ/ሰቡን መንገላታት ሰማ፡፡በእሱ ምክንያት ቀበሌው ማህበረሰብ ስቅይት ስለተሰማው ጦሩን ይዞ ወደ አባራ ጊወርጊስ ተመለሰ፡፡ ስለ ግራ አዝማች ሰማ ነጎ ጦር አሰፋፈርና ብዛት መረጃዎችን አጠናቅሮ ወደ አባይ በርሃ ወርዶ ደንብባሳ ከተባለ መልካ አደረ፡፡ሰማ ነጎ በላይ ዘለቀ አባይ ሂዷል ብሎ እንደተዘናጋ በላይም ሰማ ነጎ ያደረበትን ቤት ከቦ በማደር ንጋት ላይ የጎህ ጥቃት በመሰንዘር ሰማ ነጎና በርካታ ወታደሮችን በመግደልና ማረከ፡፡
በላይም የሰማ ነጎ እሬሳ ለመቀጣጫነት ከዛፍ ላይ እንዲሰቀል ካዘዘ በኋላ ከሞት የተረፉትንም በማሰባሰብ “ሀገራችሁን በመክዳት በጦርነቱ ከሞት የተረፋችሁ በኔ በኩል እምራችሃለሁ፡፡ ከእናንተ መካከል እናትሀገሬ የሚል ይከተለኝ  ያልፈለገም ይመለስ እናም አርሶ ይብላ፡፡ ነገር ግን ሁለተኛ ለጠላት ገብቶ የተገነ እኔ የዘለቀ ልጅ መምጣቴ ስለማቀር ውርድ ከራሴ” ብሎ አሰናበታቸው፡፡ ከዚህ በመቀጠል መጀመሪያ በልጅግ፣ዲሞትፈር ቀጥሎም መትረይስ የጦር መሳሪያ በማድረግ ጥላትን በራሱ መሳሪያ ለ5 ዓመታት ያህል መግቢያ መውጫ አሳጠው፡፡
የብቸና ከበባ ፡- 
ሚያዚያ 1930 ዓ/ም በነበላይ በተናደደው ጣሊያን ብቸና ላይ ከበባ አደረገ፡፡ የበላይን ልጅ የሽወርቅን ከእናቷጋር ማረከ፡፡ባለቤቱን ወ/ሮ ሸክሚቱ አለማየሁን ከእነ እህቷ ገደለ፡፡ እነበላይ ከጦርነቱ ሸሽተው ወደ ወሎ በመሄድ የጌት ከተባለ ቦታ ሰፈሩ፡፡በወቅቱም በላይ ማዕረግም ሰጠ፡፡አርበኞችም ተመልሰው ወደ ጎጃም መጡ፡፡
የጣሊያኖች እርቅ መጠየቅ
የበላይ ዘለቀ ተደጋጋሚ ድሎች መጎናፀፍ ጣሊያኖች እርቅ መጠየቅ ጀመሩ፡፡ለእርቅ በተፃፈው ደብዳቤ “ለጣሊያን ብትገዛ የእንደራሴነት ማዕረግ ይሰጣሃል ልጅህንም
ትመለስልሃለች” የጣሊያን መንግስት መሃሪነውና ምህረት ይደረግልሃል የሚል ነበር፡፡ በላይ በመልሱም የተላከው ደብዳቤ የላካችሁልኝ ደብዳቤ ደርሶኛል መልዕክቱንም ተረድቸዋለሁ እናም እጅግ የሚያስደስት ሆኖ አግኝቸዋለሁ፡፡ ልጀን ከመለስክልኝ እና ጎጃምን ያህል ሀገር ከሰጠኸኝ ምን እፈልጋለሁ ብሎ ምላሽ ላከላቸው፡፡ በወቅቱም በላይ አርበኞችን በመሰብሰብ እነዚህ እናስታርቃለን ብለው የመጡት ሀገራቸውን ከድተው ህዝቡን ሲያስጨፈጭፉ የቆዩ ባንዳዎች  የሰሩት ስራ ሳያሳፍራቸው ለሀገር የከዱ በመሆናቸው እናስታርቃለን ብለው የመጡትን ሽማግሌዎች መልሱን እናንተ ስጡበት ብሎ አርበኞችን አወያየ፡፡ አርበኞችም እነዚህን የሀገር ነቀርሳዎች ጊዜና ቦታ ሳይሰጣቸው ዛሬውኑ ይረሸኑ በማለት ገድለው ከዛፍ  ላይ ሰቀሏቸው፡፡
Filed in: Amharic