>

“ትግልህ ትግሌ”፣ “ደምህ ደሜ” የተባባለዉ የአማራ እና የኦሮሞ ሕዝብ (ያሬድ ደግነቱ)

  ODF : ለአንድ አማራ አስተባባሪ ግብረ ኃይል
  በ«አንድ አማራ» ድርጅት መሥራች ስብሰባ ላይ እንድንገኝ ያደረጋችሁልን ጥሪ ደርሶናል። የዛሬዉ የኢትዮዽያ ዕዉነታ በየትኛዉም መንገድ ተደራጅቶ ሀገርንና ሕዝብን ካንዣበበበት የጥፋት አደጋ ለመታደግና ለመጭው ዲሞክራሲያዊ፤ ፍትሃዊና በእኩልነት ላይ የተመሠረተ ሥርዓት መሠረት ለመጣል በጋራ መታገልን እንደሚጠይቅ ግልፅ ነዉ። በተለይም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየከፋ የመጣዉን የሕወሐት-መራሹን ገዢ ቡድን የአፈና፣ የጭቆናና እና የዝርፊያ አገዛዝ በቃኝ በማለት ሕዝባችን ያቀጣጠለዉን እና እጅግ የበዛ መስዋዕትነት የተከፈለበትን ትግል በሕዝባዊ ድል ለመደምደም በህብረት መቆም አማራጭ የለዉም። ለሚፈለገዉ ዉጤት ለመብቃት ደግሞ መደራጀት እጅግ በጣም አስፈላጊ ነዉ፡፡
የአማራ ወገኖቻችን “አንድ አማራ” በሚል ስም መደራጀት አገር ዉስጥ በሕዝባችን መካከል የተጀመረዉን አብሮ መቆም የበለጠ ለማጠናከር ብሎም “ትግልህ ትግሌ”፣ “ደምህ ደሜ”፣ “ድልህ ድሌ”፣ የተባባለዉ የአማራ እና የኦሮሞ ሕዝብ በዘላቂነት አብሮ እንዲቆምና የጋራ አገሩን በጠንካራ ዲሞክራሲያዊ መሠረት ላይ እንደ አዲስ ለመገንባት እንዲችል ያደርገዋል። የአማራን መደራጀት አስፈላጊነት እንደ የኦሮሞ ዲሞክራሲያዊ ግንባር የፀና አቋም ወስደን በተለያዩ መድረኮች ስንገልፅ የቆየነዉም የሁለቱ ሕዝብ በተደራጀ መልክ አብሮ መቆምና ለሌሎችም የአገራችን ብሔር-ብሔረሰቦች አብሮነት ምሣሌ ሆኖ መገኘት ለጊዜያዊ የፖለቲካ ትርፍ ሣይሆን ዘላቂ ለሆነ የአገር ህልዉና እጅግ በጣም አስፈላጊ መሆኑን ስለምናምን ነዉ።የአማራ ወገኖቻችንን “አንድ አማራ” በሚል ስም መደራጀት ከልብ የምንደግፈዉ ለተባበረ ህዝባዊ ትግል ከሚፈለገዉ ግብ መድረስ ከሚያደርገው አስተዋጽኦ አንፃር ብቻም ሳይሆን ድርጅቱ ተጠናክሮና በሁሉም መስክ ጎልብቶ ለዚህ ተሟጋች ላጣ ህዝብ ድምፅና ጋሻ እንደሚሆን በመተማመን ነው። ጠቅለል ባለ አገላለፅ በአማራነት መደራጀታችሁ የተያያዝነዉን ትግል በድል ለመደምደም ብሎም ለወደፊቱ የአገር ግንባታ ጥረታችን ዘርፈ-ብዙ ጠቀሜታ እንደሚኖረዉ እርግጠኞች ነን፡፡
በዚህም መሠረት በመሥራች ስብሰባችሁ ላይ እንድንገኝ ያደረጋችሁልንን ጥሪ በደስታ መቀበላችንንና ተወካዮቻችንን የምንልክ መሆናችንን እየገለፅን ጅምራችሁ ዉጤታማ እንዲሆን ለማድረግ የድርጅታችን ትብብር እንደማይለያችሁ እናረጋግጣለን።
የኦሮሞ ዲሞክራሲያዊ ግንባር #ODF
Filed in: Amharic