>

የነዳጅ አቅርቦት ለማስተጓጎል በቄሮ የተጠራ ዘመቻ (ጃዋር መሀመድ)

እንደሚታወቀው የወያኔው ቡድን በፓርላማውም ውድቅ የተደረገውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ካወጀ ወዲህ አጋዚ ወታደሮቹን በሰላማዊ ህዝብ ላይ በማሰማራት በየቀኑ ከህጻን እስከ አዛውንት ያሉ ዜጎቻችንን እየገደለ ይገኛል። እስካሁን ድረስ በነቀምቴ፣ በአምቦ፣ በደምቢዶሎ፣ በጊምቢ፣ በጊንጪ እንዲሁም ዛሬ ደግሞ በሞያሌ በርካታ ንጹሃን ዜጎች በአጋዚ ጥይት ተገድለዋል። ይህም ከፍተኛ የሆነ ቁጣ በህዝባችን ውስጥ ፈጥሯል። ስለዚህም ወያኔ ነፍሰ ገዳይ ወታደሮቹን በፍጥነት ከቦታ ቦታ በማዘዋወር ህዝባችንን እንዳይፈጅ እንቅስቃሴውን ለመግታት ብሎም የመጨቆኛ አቅም ለማዳከም የነዳጅ አቅርቦት የማቋረጥ እርምጃ እንዲወሰድ የሚያስገድድ ሁኔታ ተፈጥሯል ።

በዚሁ መሰረት ከመጪው ማክሰኞ መጋቢት ፬ እስከ ሰኞ መጋቢት ፲፥ ፪ሺህ፲ ዓ.ም. (ከማርች 13 እስከ ማርች 19, 2018) ድረስ ለአንድ ሳምንት የሚቆይ የነዳጅ አቅርቦትን ለማስተጉዋጎል እርምጃዎች ይወሰዳሉ። የነዳጅ ማመላለሻ ተሽከርካሪዎች ከውጭ ሃገር ነዳጅ ጭነው ወደ ሃገር ውስጥ እንዳይገቡ፣ ሃገር ውስጥም ነዳጅ ጭነው ከቦታ ቦታ መንቀሳቀስ እንዳይችሉ ይደረጋል። ይሄን ማዕቀብ ጥሰው በሚንቀሳቀሱ የነዳጅ ማመላለሻ ተሽከርካሪዎች ላይ እርምጃ ይወስዳል። ዝርዝር አፈፃፀሙ በቅርብ ይገለፃል።

ጥንቃቄ:

ዘመቻው በጥንቃቄ የሚካሄድ ይሆናል። የሚወሰደው እርምጃ በከተሞች ውስጥ ያሉ የነዳጅ ማደያዎችን አይመለከትም። የዚህ ዓይነቶቹን ተቋማትን ላይ የሚወሰድ እርምጃ የንጹሃን ህይወት ላይ ኣደጋ ስለሚያስከትል ነው:: የዚህ ዓይነት ተግባራትን በመፈጸም የህዝቡን ትግል ለማጠልሸት ስርዓቱ የሚያሰማራቸውንም አካላት በመከታተል እኩይ አላማቸውን ለማክሸፍ በትጋት የሚሰራ ይሆናል።

በመጨረሻም ህዝባችን ይሄንኑ ተገንዝቦ አስፈላጊውን ዝግጅት እንዲያደርግ ከወዲሁ እናሳስባለን። የነዳጅ ማመላለሻ አሽከርካሪዎችም ይሄንኑ እንድትገነዘቡና ተገቢዉን ጥንቃቄ እንድታደርጉ ትመከራላቹ። ይሄንን ተላልፋቹ ራሳቹን ለአደጋ እንዳታጋልጡም ከወዲሁ እንመክራለን።

ሰፊው ሕዝብ በትግሉ ድልን ይጎናጸፋል!!

Filed in: Amharic