>

የኦሮሞ ህዝብ ትግል በዕውቀትና በስሌት እንጂ በስሜት መመራት የለበትም። (ብርሃነመስቀል አበበ)

ህወሃት በህዝባችን ላይ የከፈተውን አጠቃላይ ጦርነት በድል ለመወጣት በእውቀትና በስሌት ላይ የተመሠረተ ተመጣጣኝና ሁሉ አቀፍ ራስን የመከላከል ስልትና ስትራቴጂ ያስፈልጋል። ትግሉ በእውቀት፣ በስሌትና በድርጅት እንጂ በስሜት የሚመራ መሆን የለበትም። ትግሉ መንገድ ላይ ወጥቶ ከመሞት የጀብደኝናት ስነልቦና መውጣት አለበት።  በጠላት ላይ የኢኮኖሚ፣ የፓለቲካና የስነልቦና ኪሳራና ጉዳት ማድረስ እና ወገንን ከጥቃትና ከሞት መከላከልና ህዝባችንን ለድል ማብቃት የሚወጡት ህዝባዊ የትግል ስልቶች ሁሉ ግንባር ቀደም ተልዕኮና አለማ መሆን አለባቸው። በዚህም መሠረት፣

1ኛ፣ ህወሃት በህገ ወጥ  የአስቸኳይ ጊዜ አወጅ ሽፋን በኦሮሞ ህዝብ ላይ  ያወጀው  አጠቃላይ ጦርነት አንዱና ዋነኛ ኢለማ በፕረዚደንት ለማ መገርሳ የሚመራውን ተራማጅ ቡድን ከኦሮሞ ህዝቡ በመነጠል መምታት ነው።የትኛውም ኦሮሞ ሆነ የተቀረው የኢትዮጵያ ህዝብ ይህን ከሳተ የህወሃትን የጦርነት ስልት አላወቀም ማለት ነው።  በ201 የፓርላማ አባላት ድምፅ በመነፈጉ ምክንያት ውድቅ በተደረገው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ዙሪያ በነበሩት ውይይቶች ላይ በተወሰዱ ግልፅ የስትራተጂ ስህተቶች ምክንያት ፕረዚደንት ለማንና እርሱ የሚተማመንባቸውን የቡድኑ  መሪዎች ላይ ከህወሃት ጋር አንድ ወገን ሆኖ ማጥቃት፣ስም ማጥፋትና እነዚህን መሪዎች ከኦሮሞ ህዝብ መነጠል፣ የኦሮሞ ህዝብን ትግል ከህወሃት ጋር ወግኖ ከማጥቃት ምንም ልዩነት የለውም።የአንድ ጄኔራል የጦር ውሎ በአንድ የጦር ግጥሚያ   ስላፈገፈገ፣ የተሳሳተ ውሳኔ ስለወሰነ ወይም በጠላት ስለተሸነፋ የራሱ  ወገን ጦርነት አይከፍትበትም። ወይም ዘራፍ ብለህ ለምን አልሞትክ አይባልም። በመሪህ ደረጃ የሁሉም ሰው ህይወት እኩል ነው። በጦር ሜዳ  ውሎ ግን የአንድ ጄኔራል መሞትና የአንድ ተራ ወታደር መሞት እኩል አይደለም።በፓላቲካውም አለም የአንድ  አገር መሪ መሞትና የአንድ ዜጋ መሞት እኩል አይደለም። በሰዋች አለም ይቅርና በንቦች አለም እንኳን የአንድ የንግስት ንብ መሞትና አንድ የተራ ንብ መሞት ለአንድ የንብ መንጋ እኩል አይደለም። መሪዎቻችን ደፋርና ቆራጥ እንዲሆኑ ማበረታታቱ እንዳለ ሆኖ ለምን ዛራፍ ብለው አልሞቱም ብሎ መተቸት ግን  ሌላ ነገር ነው። በዚህ ጉዳይ ላይ የኦሮሞ ህዝብ የፕሬዚደንት ለማ መገርሳን ውሳኔና አመራርን መክበርና መከተል አለበት።ክቡር አቶ  ለማ መገርሳ  የተማመነውና የማይነጥፍ ቃሉን አምኖት የሰጠው የኦሮሞ ህዝብ ለህወሃት ጅቦች እርሱንና የሚተማመንባቸውን አጋሮቹን ጥሎ ከእነርሱ በዚህ የቁርጥ ቀን መሸሽ የለበትም። መካካድ የኦሮሞ ህዝብ ባህሪም፣በህልም አይደለም።የኦሮሞ ህዝብ የዘመናት ትግል የወለዳቸውን መሪዎች እንደ ባንድራ ጠዋት ሰቅሎ ማታ አያወርድም።መሪዎቻችን በራሳቸው የመተማመንና በህባቸው የመተማመን ስነልቦና እንዲጎለብት የመሳሳትና ስህተታቸውን የማረም ቦታና ጊዜ ልንሰጣቸው ይገባል። ከተቺዎቹስ ያልተሳሳተ አለ እንዴ?  ስለዚህ አቶ ለማ መገርሳ በሚታመንበትና የኦሮሞ ህዝብን ወክሎ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር እንዲሆን ሰይመነዋል ብሎ ለመላው የኦሮሞ ህዝብ በስም ጠርቶ በተነገረው ዶ/ር አብይ አህመድ ላይ የተከፈተው የስም ማጥፋትና ዶ/ር አብይን ከኦሮሞ ህዝብ የመነጠልና የፓለቲካ ፋይዳ የማሳጣት ዘመቻ በአስቸኳ መቆም አለበት።ዶ/ር አብይ በአስቸኳይ ግዜ አዋጁም ላይ ድምፅ ያለመስጠቱ በራሱ ትልቅ ውሳኔ መሆኑ ልታወቅ ይገባል። ስለዚህ  የኦሮሞ ህዝብና የኦሮሞ መሪዎችም  አስቸኳይ የፓላቲካ  እርምት በመውሰድ የደረሰውን ጥፋት መቀልበስና መሰል ጥፋት እንደይደገም አስቸኳይ  እርምጃ  መውሰድ አለባቸው።

2ኛ፣ የኦሮሞ ህዝብ በህወሃት የተከፈተበትን አጠቃላይ ጦርነት በድል ለመወጣት  የአጭርና የረጅም ጊዜ እቅድ አውጥቶ ወደሚሰራበት ደረጃ መሸጋገር አለበት።ፓላቲካ በእውቀትና ስሌት እንጂ በስሜት የሚመራ ያለመሆኑ መታወቅ አለበት። ስለዚህ ህወሃት በጅምላ ሰው ልገል የሚችልባቸውን እንደ ሰላማዊ ሰልፍ አይነት ስልቶች ማተው አለባቸው። ሰው በማስገደል ድል የለም።  ትግሉ ከትጥቅ ትግልም ይልቅ  የኢኮኖሚ፣ የፓላቲካና የስነ ልቦና ነው። ስለዚህ ህወሃት በኢኮኖሚ፣ በገንዘብ፣ በፓላቲካና በስነ ልቦና ማክሰር የትግሉ ትልቅ አካል መሆን አለበት። ህወሃት ታጣቂዎቿን በየኦሮሚያ ቀበሌዎች ብታሰፍር ቢበዛ ከአንድ አመት በላይ ስንቅና ትጥቅ ሰጥታ ማቆየት አትችልም። የኦሮሞ ህዝብ በእምብተኝነትና በዝምታ ብቻ ህወሃትን አክስሮ ማሸነፍ ይችላል።  በተጨማሪም  ህወሃትን መንገድ እየመሩ ህዝባችንን የሚያስገድሉ ባንዳዎችን ማጥፋት አስፈላጊ ነው። የህወሃት የኢኮኖሚ መሠረት የሆኑትን  ቡድኖች ከህዝባችን መሃል መንቀል ይገባል። የኦሮሞ ወታደሮችና የፀጥታ ሰዋች ከኦሮሞ ህዝብ ጋር እንዲቆሙ ማድረግ አለብን። የአከባቢ ፓልስና ሚሊሻ ማጠናከርና የህወሃት ታጣቂዎች በቀንም ሆነ በለሊት በህዝባችን ላይ የሚያደርሱትን ጥቃት ተባብሮ መከላከል አስፈላጊ ነው።

3ኛ፣በኦሮሞ ህዝብ ላይ የጅምላ እልቂት እንዲካሄድ የወሰኑትና ያስወሰኑትን የኦሮሞ የፓርላማ አባላት በሙሉ የኦሮሞን ህዝብ ስለማይወክሉ እንወክለዋለን የሚሉት አከባቢ ህዝብ በአንድ ድምፅ እንዲያባርራቸው ማድረግ። እነዚህ አባላት አሁን በስም ስለሚታወቁ ከኦህዲድ መዕካላዊ ኮሚቴ፣የሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴና ከድርጅቱ አባልነት ማባረር።  በተጨማሪም ለእነዚህ ግለሰቦችና ቤተሰቦቻቸው ኦሮሚያ ውስጥ አዲስ አበባን ጨምሮ እንኳን መኖሪያቸው፣ መቀበሪያቸው እንዳትሆን በህዝብና አገር ክህደት ከሶ በህግ ማስከልከል ይገባል።

4ኛ፣ የፕረዚደንት ለማ አመራርም በአስቸኳይ የኦሮሚያን ፓርላማ ጠርቶ በኢትዮጵያ ህገ መንግስት አንቀፅ 39 ንዑስ አንቀፅ 1 እና 2 መሠረት የኦሮሞ ህዝብ ራስን በራስ የማስተዳደር መብት እንዲከበርና በህወሃት የሚመራው ጦር ከኦሮሚያ እንዲወጣ መጠየቅ አለበት። በህገመንግስቱ አንቀፅ 39 የተቀመጠው ራስን በራስ የማስተዳደር መብት በአስቸኳይ ግዜ አዋጅ የማይነካ በህገ መንግስቱ የተረጋገጠ የኦሮሞ ህዝብ መብት ነው። ህገ ወጡ የህወሃት አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ  ይህን የህገ መንግስቱን አንቀፅ አይሽርም። ስለዚህ  የኦሮሚያ ምክር ቤት ይህን አንቀፅ ተጠቅሞ የህወሃት ታጣቂዎች  በኦሮሚያ  የሚያደርጉትን ጣልቃ ገብነት ሙሉ በሙሉ እንዲያቆሙና  የኦሮሞ ህዝብን የራስን በራስ የማስተዳደር መብት መጋፋት እንዲያቆሙና ከኦሮሚያ እንዲወጡ መጠየቅ አለበት። ይህ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የማይነካውና የማይሸራረፈው አንቀፅ የብሄሮችን ራስን በራስ ማስተዳደር መብት አልፎ እስከ መገንጠል መብት የሚሰጥ መሆኑ ይታወቃል። ለኦሮሞ ህዝብ ኢትዮጵያ በደሙና በአጥንቱ የገነባት አገሩ ነች። መገንጠል የህባችን አላማም፣ ሃሳብም አይደለም። ራስን በራስ ማስተዳደር ግን ማንም የማይዳፈረው የህዝባችን የተፈጥሮ መብት ነው። ስለዚህ የኦሮሚያ ፓርላማ በአስቸኳይ ተሰብስቦ በአንቀፅ 39 መሠረት የኦሮሞ ህዝብን ራስን በራስ የማስተዳደር መብቱን ማስከበር  አለበት። የኦሮሞ ህዝብ ይህን መብቱን ለማስከበር ከኦሮሚያ ክልል መንግስት ጋር ተባብሮ ይሰራል።

5ኛ፣ የኦሮሞ የፓርላማ አባላት አስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ውድቅ በማድረግ የሰጡትን  ድምፅ  በመሻር አዋጁ አልፏል ብሎ በህወሃት ጀሌዎች መነገሩ የአገርና የህገ መንግስት  ክህደት ወንጀል ነው። የኦሮሚያ ክልል መንግስት የኦሮሞ ፓርላማ አባላት ድምፅ ሳይከበር ሲቀርና ህገ መንግስታዊ ስራኣቱ ሲናድ በዝምታ መመልከት የለበትም። በመሆኑም የኦሮሚያ ክልል መንግስት የኦሮሞ ህዝብ በኢትዮጵያ ፓርላማ  የመረጣቸው እንደራሴዎቹና ተወካዮች የተሰጠውን ድምፅ በመጣስ ተላለፈ የተባለው ህገ ወጥ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እንዲሰረዝ በፌድራል ጠቅላይ ፍ/ ቤት ክስ መመስረትና በአዋጁ ላይ የመጫረሻ  ውሳኔ እስኪሰጥበትም ፍ/ ቤቱ አዋጁን እንዲያግድ መጠየቅ አለበት። ለዚህም  የክልሉ መንግስት አንድ የጠበቆች ቡድን አቋቁሞ በአስቸኳይ ክስ መመስረት አለበት። የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን የተቃወሙት የኦሮሞ የፓርላማ አባላትም ይህን ክስ በጋራ ማቅረብ ይችላሉ። ህወሃት በሚቆጣጠራቸው የመገናኛ ብዙሃን እና ጀሌዎቹ ስለዋሸ  በህገ መንግስቱ መሠረት ውድቅ የተደረገ አዋጅ ህግ አይሆንም። የኦሮሞ ህዝብና የክልሉ መንግስት  ህገ መንግስታዊ ስረዓቱን ማስከበር አለበት። ስረዓቱ ተፈትሾ  የህግ የበላይነትን  ማስከበር እንኳን ባይቻል   የህወሃትን ሌብነት፣ ባዶነት ወንጀለኛነት ለአለም አሳይቶ መገርሰስ ትልቅ የፓላቲካ ድል ነው።

6ኛ፣ የኦሮሞ ተቃዋሚ ድርጅቶች በተለይም የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረስ አባላትና ደጋፊዎች እንዲሁም የውጭና የአገር ውስጥ የኦሮሞ አክቲቪስቶች መላውን የኦሮሞ ህዝብ በማስተባበር ያለምን የፓላቲካ ልዩነት ከፕረዝደንት ለማ መገርሳና እርሱ ከሚሰጠው አመራር ጋር መቆም አለባቸው። መከፋፈል፣ መጠቃቃት፣እና ስም መጠፋፋት ህወሃትን መርዳት እንጂ ሌላ ፋይዳ የለውም።አሁን ጊዜው የጦርነት እንጂ የፓለቲካ አቃቅር ማውጫ ጊዜ አይደለም። ስለዚህ ከነጉድለታችንና ድካማችን ተጋግዘንና ተባብረን ይህን አውሬ ማሸነፍ አለብን።

7ኛ፣ የእነ አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ቡድን ተዳከመ እንጂ አልተሸነፈም። መለው የአማራ ህዝብ የአውሬውን ቡድን በመላ አማራ እንዲያሽመደምድ ከኦሮሞ ህዝብ ጋር  የተጀመረውን ትብብር ማጠናከር አለበት።  የአማራና የኦሮሞ ወጣቶችን ትስስር በጋራ ራዕዎችና ጥብቅ ወንድማማችነት ላይ እነዲገነባ ጠንክሮ መስራት ያስፈልጋል። የኦሮሞና የአማራ ህዝብ ህወሃት የሚዘራቸውን የመካካድና የመጠራጠር ዘሮችን ሰይበቅሉ ማጥፋት አለበት። ትግሉ ተከታታይና ረጅም ጊዜ ሊወስድ እንደሚችል  በመገንዘብ  ሁሉም ኢትዮጵያዊ የህወሃትን የኢኮኖሚ፣የፓላቲካ፣የፀጥታ መረቦችና ማህበራዊ መሠረቶች በየደረጃው እንዲያፈርስ ማድረግ  ይገባል።

 

Filed in: Amharic