>

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ፀደቀ ተባለ? (ደ/ር ታደሰ ብሩ)

ህወሓትን ለማዳን ሲባል በኢትዮጵያ እና በኢትዮጵያዊያን ላይ የሚደረገውን ፍጅት ህጋዊ የሚያደረገው “የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ” በ346 አባላት ድጋፍ፣ በ88 ተቃውሞና በ 7 ሰዎች “ከደሙ ንፁህ ነን” ድምፀ ተዓቅቦ ፀድቋል ተብሏል።  እንደሚታወቀው ፓርላማው 547 መቀመጫዎች አሉት። ይህ ህግ የፀደቀው ከፓርላማው መቀመጫዎች 2/3ኛ ሳይሆን በዕለቱ ከተሰበሰቡት 2/3ኛ  ስሌት መሆኑን ለትዝብት ያህል በማስገንዘብ ወደሌሎች ጉዳይ ልለፍ።
ከሁሉ አስቀድሜ የተቃወሙት 88 እና ድምፀ ተዓቅቦ  ያደረጉት 7 በድምሩ 95 ሰዎች በዚህ ፓርላማ ውስጥ መገኘታቸው በኢህአዴግ አባላት ሙሉ በሙሉ ተስፋ ከመቁረጥ ታግዶናል ብዬ አምናለሁ። እነዚህን ወገኖች በተለመደ ህወሓታዊ መሰሪ “ድርጅታዊ ሥራ” ምርጫውን ዲሞክራሲያዊ ለማስመሰል ተቃወሙ ተብለው ታዘው እንዳልተቃወሙ ተስፋ አደርጋለሁ። እኔ በዚህ ፓርላማ ውስጥ ይህን ያህል ተቃውሞ ይኖራል ብዬ አልገመትኩም ነበር። እነዚህ ወገኖች የተቃወሙት በራሳቸው ውሳኔ ከሆነ “እንኳን ደስ ያላችሁ” እላለሁ። ምንም እንኳን ዛሬ በአድርባዮች ብዛት ተሸንፋችሁ ህጉ ቢያልፍም እናንተ የተቻላችሁን አድርጋችኋልና ክብር ይገባችኋል፤ እናከብራችኋለን።
ይህ አዋጅ ለህወሓት የሚኖረው ትርጉም “በቅሎ ገመዷን በጠሰች ቢሉ በራሷ አሳጠረች” እንደተባለው ነው። አዋጁ ከሁሉም በላይ የሚጎዳው ህወሓትን ነው። አዋጁ ጮሆ የሚናገረው ህወሓት መለወጥ የማይችል በዚህም ምክንያት መጥፋት ያለበት ድርጅት መሆኑን ነው።
ከእንግዲህ ምን ይደረግ ?
1. ሕዝባዊ እምቢተኝነቶች ቀድሞ ከነበረው እጅግ በተባባሰና በተጠናከረ ሁኔታ ይቀጥሉ፤ በሕዝባዊ እምቢተኝነት ሥርዓቱ መሽመድመድ አለበት፣
2. ሕዝባዊ እምቢተኝነቶች ራስን ከጥቃት በመከላከል ተግባራት ይታጀቡ፤ ዝም ብሎ  መሞት፣ መገረፍ፣ መታሰር፣ መጋዝ መቆም አለበት፣
3. በሥርዓቱ ላይ ሕዝባዊ አሻጥሮችን መሥራት የዕለት ተዕለት ኑሮዓችን አካል ይሁን፤ ከፋሽስት ህወሓት ሥርዓት ጋር መተባበር የተወገዘ  ይሁን፣
4. የኅብረተሰብ ክፍሎችና የተለያዩ እምነቶች ተከታዮች ኅብረቶች ይጠንክሩ፤  ነፋስ በመካከላችን አይግባ፤ የጎንዮሽ አተካራዎች ቆመው ፍላፃዎች ሁሉ ህወሓት ላይ ያነጣጥሩ፣
5. ለመከላከያ ሠራዊት አባላት ተደጋጋሚ ጥሪዎች ይደረጉ፤ አፈሙዛቸው በአለቆቻቸው ላይ እንዲያዞሩ ይበረታቱ፤ አዳዲስ ተመልማዮች እንዳይኖሩ ይደረጉ፣
6. የህወሓት ሰላዮች ሕዝብን መሰለላቸው አቁመው አለቆቻቸውን እንዲሰልሉ ይበረታቱ፣
7. ህሊና ያላቸው የኢህአዴግ አባላት ወደህሊናቸው ተመልሰው የሕዝብን ትግል እንዲያግዙ ጥረት ይደረግ፣
8. ከህወሓት በኋላ የሚመጣው ሥርዓት ለሁላችንም የምትመች ኢትዮጵያ መሆኗን የሚያረጋግጡ ሥራዎች ይሠሩ፣
9. አዋጁ የድሉን ዋጋ ከፍ ቢያደርገውም ጊዜውን ግን አቅርቦታልና ሁላችንም የየበኩላችን ተግባራዊ ተሳትፎ  እናድርግ፡
Filed in: Amharic