>

“አንዳርጋቸው ጽጌ መንፈስ ነው።” ከጸጋዬ ገብረመድህን አርአያ (ጋዜጠኛ ሙሉጌታ ሉሌ)

የአንዳርጋቸው “ሌጋሲ”– የትውልድ ቅርስ፣የትግል ቅርስ …የመስዋዕትነት ቅርስ  ነው!!!

“አንዳርጋቸው ጽጌ መንፈስ ነው።”

ከጸጋዬ ገብረመድህን አረአያ ~ (ጋዜጠኛ ሙሉጌታ ሉሌ)

በ1950 ዓ.ም. ደብረብርሀን በሚገኘው የሀይለ ማርያም ማሞ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ስገባ የዓጼ ዘርአ ያዕቆብ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ዳይሬክተር የነበሩት አቶ ጽጌንና ባለቤታቸውን በየቀኑ አያቸው ነበር። ወይዘሮ አልታዬ ዘወትር በቀኝ እጃቸው እየደገፉት እሱ ድክ ድክ የሚልም ትንሽ ልጅ አይረሳኝም። የየዕለቱ ትርኢት ስለነበር . . . . ብዬ አልፌዋለሁ።

ከዘመናት በኋላ እኔም አድጌና በመንግስት ስራ ኃላፊነት ቆይቼ ይህቺን አገር የሚያናውጡ ሰዎች ወደ ፖለቲካው መድረክ ሲመጡ በመጥረጊያ ከተጠረጉት የጥንት ጋዜጠኞችና የሚዲያው አመራር አባላት ጋር እዳሪ ስንጣል ያ ልጅ ይመስለኛል ከጦቢያ ቢሮ ያገኘኝ። አንዳርጋቸው ጽጌ ከመቼው በወያኔ መርከብ ተሳፍሮ ፣ ከመቼው ወርዶ፣ ከመቼው ወደ ተቃዋሚነት እንደተሸጋገረ የፖለቲካው ጉዞ ቅፅበት አልገባኝ አለ። የተቀላቀለው ቡድን አካሄድና ይልቁንም “አማራ” በተባለው የህብረተሰብ ክፍል ላይ ያለውን ግልጽ አቋም በመረዳት “የአማራው ህዝብ ከየት ወዴት?” የሚል መጽሀፍ ጽፎ ለህዝብ ሲያቀርብ እኔም ሆንሁ ብዕሩ እልፍ የሚጥለው ጓደኛዬ ሰውነት መልካሙ ጥርጣሬ ውስጥ ወድቀን ነበር። ስለዚህ ሰውነት (በብዕር ስምነት ይቆይና) “በኢትዮጵያዊነት ላይ የተወረወረ ቦምብ” በሚል ርዕስ የራሱን ቦምብ አፈነዳ። አንዳርጋቸው አስተያየት የመስጠት መብታችንን እየጠቀሰ በመሰረቱ ግን “አቶ ሰውነት ትክክለኛው ጉዳይ የገባቸው አይመስለኝም” ብሎ ከእኔ ጋር በጦብያ ቢሮ (አክፓ ክ ነው እንባል የነበረው) ደስ የሚልና ምሁራዊ ቅባት የነበረበት ሙግት ገጠምን። ድር። በእኔ በኩል ይህን ድርጅት ፋሽስት ለማለት የፈለግሁት ኢሰብዓዊ አቋሙን ፣ ደም የማፍሰስ ሱሱን፣ ለህይወት አንዳች ዋጋ ለመስጠት ያለመፈለግ ዝንባሌውን . . . ለማሳየት ነበር።

አንዳርጋቸው ደግሞ የተማሪው ፖለቲካ ፍሬ እንደመሆኑ ወደ ክላሲካል ትርጉሙ ለመሄድ ነበር የፈለገው። በነገራችን ላይ አንዳርጋቸው በችኮላ ላይ ስለ ነበርና ጊዜም ስላልነበረው ስለፋሺዝም ብዙ ሳንወያይ ተለያየን። ጊዜ ቢኖረው ኖሮ “አብዮታዊ ዴሞክራሲ” ከቤኒቶ ሙሶሊኒ “አቫንቲ” እና ከፋሽዝም የተዳቀለ መሆኑን (ያው መጻህፍት በመጠቃቀስ) አስረዳው ነበር። የተማሪ ፖለቲካና የሶቭየት (ኢምፓየር) ቀኖናውያን እንደሚሉት “ ቀኝ ክንፍ ፍልስፍና ” (ኢዲዮሎጂ) አለመሆኑን ለማብራራት እሞክር ነበር። በነገራችን ላይ ሙሶሊኒ ሮጦ ከሂትለር ክንፍ ሥር ሳይወድቅ የምዕራቡ ዓለም መሪዎች (እነ ሩዝቬልትና የውጪ ጉዳይ ሚኒስትሩ ሐል) ፋሺዝምን እንደ ታላቅ የዓለም ፖለቲካ የዕድገት ማስረጃ አድርገው ያዩት ነበር። ፋሺዝም የመጣው እንደ ሬቮሉሲዮን ስለሆነ የቀኝ ክንፍ ፍልስፍና አይደለም። ይህ ክርክር ያልተፈጸመና በአጭሩ የቀረ ጭንጋፍ ሙግት ነው። አንዳርጋቸውን በዚህ ዓይነት ሙግት የምዘርር አይደለሁም። እሱ ላቅ ያለ አመለካከትና ትንፋሹ ሳይቀር ሕይወት ያለው ነው። በዓለም አቀፍ የቅንጅት ኮሚቴ ውስጥ አብረውት የሠሩ ዘመዶችና ወዳጆች አሉኝ። ይሳሱለታል። “አንዱ . . .አንድዬ . . . አንዳርግ . . .” ይሉታል። የቅንጅት አመራር አባላት በወያኔ ወኅኒ ዓለም በተወረወሩ ጊዜ በሳምንት ውስጥ ለቢቢሲ ሰባት ቀናት መግለጫ ሲሰጥ ሰምቼዋለሁ። በበሰለ አሳብ ፣ በጠራ ቋንቋና በጨዋ አንደበት። ይህ ብቻም አልነበረም ፤ በወቅቱ የአፍሪካ ህብረት ዓመታዊ ስብሰባ በአክራ ሲካሄድ የጋናን ሚዲያ በተለይ፣ እና የአፍሪካ መገናኛ ብዙሀንን በአጠቃላይ በቁጥጥሩ ስር አውሎ በኢትዮጵያ ላይ እየተካሄደ ያለውን የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚ፣ የማህበራዊ ባህል በሚያስደንቅ አኳኋን ሲያቀርብ የነበረ ጀግና ነው። አንድ መቶ የፕሮፖጋንዳ ሰራዊት የማይችለውን የአትላስ ሽክም ብቻውን በአስገራሚ ሁኔታ ያከናወነ ልዩፍጥረት ነው።እኔ ደግሞ የዚህን ሥራ አስቸጋሪነት በልዩ ልዩ ገጽታው አውቀዋለሁ ባይ ነኝ። “ተራራ አንቀጠቀጥን . .” የሚሉ የመሣርያ አምላኪዎችና ባሩድ ነካሾች ይህን ታላቅ ነፍስ-የኢትዮጵያ ነፍስና ከኢትዮጵያ ጎን የወጣ ልጅ -ከአስመራ እስከ ዱባይ…ከየመን እስከ ደቡብ አፍሪካ….ከእንግሊዝ አገር እስከ አሜሪካ ወዘተ ባሰማሯቸው የስለላና የአፈና ጓዶች አማካኝነት ዓለምን ሲያካልሉ ከርመዋል። ቁጥር ስፍር የሌለው ገንዘብም አፍስሰዋል።

በመጨረሻም ዱባይ፣አስመራ፣ደቡብ አፍሪካ ያሉት የቆስጤ ሴረኞች … የምስራች ተባብለዋል። እነሆ ውቡ ወፍ ተጠምዷል። የትግሉም ሆነ የዓለምም ፍጻሜ ግን አይደለም። አይሆንምም። አንዳርግ የከፈለው ሰማዕትነት በሚቀጥሉት የኢትዮጵያ ትውልዶች በክብር ይወሳል። ለአዲሱ ዘመን አውራ ጀግና በማግኘታችን ልንኮራ ይገባናል።

እግዚአብሄር ይከበር-ስለአንዳርጋቸው! አገሮች በታሪካቸው ትልልቅ ፈተና ያጋጥማቸዋል ። ሕዝብ በችግር ሰዓት ይጠራራል። እንደዚህ ላስቀምጠው። – በጭንቅ ሰዓት ፣ በፈተና ጊዜና ቀን የጎደለ በሚመስልበት ወቅት ከማዕበሉ ጋር የሚታገልና ድልን የሚያስገኝ ፤ ካልተሳካም በድፍረቱ ፣ በልበ ሙሉነቱ ይህን ያህል የማይባል ረቂቅ ድልን የሚያቀዳጅ ሰው ይሻል። በደሙና በማይነገር – በማይበገር ጥንካሬው አማካይነት ወጀቡን የዋኘ ፣ ማዕበሉን ጸጥ ያደረገና የሚያደርግ ፤ ለዛሬው ትውልድ የነጻነት ብልጭታ ያሳየ (የሚያሳይ) ፤ ለመጪው ከውስጡ ብርሀኑ ቦግ ያለ የትግልን ችቦ የሚያቀብል (ያቀበለ) ሰው ይሻል።

የህንድ የመጀመሪያው ጠቅላይ ሚኒስትር ጀዋህርላል ኔህሩ በታላቁ የዓለም ሰው በማህተመ ጋንዲ (በአክብሮት ጋንቲጂ) ሥርዓተ ቀብር (በሂንዱ ልማድ ቀብር ሳይሆን የማቃጠል ሥርዓት ነው ያለው) ላይ ሲናገሩ የተጠቀሙበትን አንድ ሐረግ ልሰርቅ አፈልጋለሁ። ለአንዳርጋቸው ጽጌ ለመስጠት! “ጋንዲ ልዩ አፈር ነው። ከእኛም ልዩ የሚያደርገው ልዩ አፈርነቱ ነው።” ብለዋል። እኔ ራሴ መንቀሳቀስ የማይሆንልኝና በማንኛውም የአገሪቱ ታሪክ ላይ ይህ ነው የሚባል አሻራ ለማሳየት የማይሆንልኝ ቧጋች ነኝ። ሰዎችን የማወቅ ዕድል ግን አለኝ። ጀግና ብቻ ሳይሆን ባንዳና ምንደኛም አውቃለሁ። ተጎልቼ ይህን የመሳሰለውን ወግ እጠርቃለሁ። አላጋንንም።

አንዳርጋቸው እንደማናችንም ከአፈር -ከኢትዮጵያ አፈር ተፈጥሯል። እእ! ከኢትዮጵያ ልዩ አፈር! ስለዚህ ‹ልዩ ሐረግ› የኔህሩን ሽንት ይባርክ! የአንዳርጋቸው ጠላፊዎችና አሳሪዎች የጀግና መንፈስ የላቸውም እንጂ በክብር የሚጠብቁት ልዩ እንቋቸው በሆነም ነበር። ሚኒልክ የጎጃሙን ንጉስ ምርኮኛቸውን የተንከባከቧቸው በክብር በመጠበቅ ነበር። ወያኔዎች ከፈሪ ልብ የተቆረጡ ፈሪዎች በመሆናቸው እንጂ አንዳርጋቸውን ያንን ያህል የስጋ ስቃይ ባላደረሱበት ነበር። ለትርዒት መላልሰው ባላቀረቡትና የደስታቸው ምንጭ ባላደረጉትም ነበር። እነሱ ዛሬ የሥጋ ቁስልና የመንፈስ ስቃይ የሚግቱት ሰው ነገ የታሪካቸው ፈርጥ የሚሆን ልዩ አፈር ይሆናል።

ሃሌሉያ! በአጠቃላይ አንዳርጋቸው የነጻነት ተጋድሎውን የተወጣ ፤ ምድራዊ መከራን፣ አካላዊና መንፈሳዊ ቅጣትን ሁሉ የተቀበለ፣ትግሉን ለሌሎቻቸን በአደራ ያስተላለፈ ታላቅ ነፍስ ነው። ታላቁ ህንዳዊ ጋንዲ “ማሀትማ” ይባላል። “የተከበረ ነፍስ” ማለት ነው። የዓለም ጌታ እንዳለው ነቢይ በአገሩና በዘመኑ አይከበርም ሆነና አንዳርጌ የሚገባውን አክብሮትና አድናቆትን ጠላት በተንጣለለበት አገሩ ለማግኘት ባይችልም በውጪው ዓለም የተበተኑና የውስጡንም የሚወክሉ ወገኖች ሁሉ ህዝብ ለማንም ሰጥቶ የማያውቀውን ክብር ሰጥተውታል። የኢትዮጵያ ጆን ኦፍ አርክ፣ የኢትዮጵያ ማንዴላና ጋንቲጂ ብለውታል። ጠላቶቹ የአገር አጥፊዎች እየተዘባበቱበት፣ እየሰደቡትና እንደ “ጊኒ ፒግ” መላልሰው በቴሌቪዥ ን እያቀረቡት ነው። ልዩ ወፋችንን—ናይቲንግኤላችንን ባሰቡ ቁጥር መንፈሳቸውን የሚያሸብር አንዳች ስሜት ተጣብቷቸው ቆይቶ መያዙንና በእጃቸውመግባቱን ያለማመን ችግር ደርሶባቸዋል።

“ሶባጅ – ሳቬጅ!” ፍሬደሪክ ኤንግልስ ወዳጁና ጓዱ ስለነበረው ካርል ማርክስ በቀብሩ ሥነ ሥርዓት ላይ የተናገረው ምስክርነት ትዝ ይለኛል። The best hated man ይለዋል። (ከሁሉ የበለጠ የተጠላ ሰው እንደማለት ነው።) በወቅቱ በተፈጠሩም ሆነ በኋላ በተነሱ ትውልዶች ዘንድ ግን ካርል ማርክስ The best hated man ብቻ ሳይሆን The best loved man ሆኗል።

አንዳርጋቸው ጽጌ በእጃቸው በገባ ሰዓት ማራኪዎቹ ወያኔዎች የተሰማቸውን ደስታ ጣኦታቸውና የሴረኞች ሁሉ አባት የሆነው አምባገነን ከሞተበት ዕለት ኅዘን ጋር ማስተያየት ይቻላል። አዎን አንዳርጋቸው በወያኔዎች ለወያኔዎች የቀትር ጋኔን ነበር። የሚያስፈራ ነፍስ – እንኪያስ The most hated man ለኢትዮጵያ ሰፊ ህዝብ ደግሞ The most loved man! ይታደለዋል እንጅ …በዚህም መሰረት ይቀጥላል።

አበበ አረጋይ …በላይ ዘለቀና አሞራው ውብነህ፣ ጅማ ሰንበቶ፣ በቀለ ወያ፣ አብዲሳ አጋ ሲደመር ሲደማመር ቅዱስ ያሬድ፣ ዮፍታሄ ንጉሴ፣ ዶክተር ዓለመወርቅ . . . ነው። አላበዛሁበትም ። ክብር ሁሉ አልከመርኩበትም። ቢሆንልኝ ከነጋ ድራስ ተሰማ እሸቴ ጋር “እንደምን አድርጌ ከፍቼ ላውጣው” እያልኩ አቀነቅን ነበር።

ጀግኖች የኢትዮጵያ ወጣቶችና ጸጥ ወዳለው ዓለም የምትሸጋገሩ አእሩግ! ናፖሊዮንም ተማርኳል። ታላቁ ጄነራልና ጦረኛ መሪ። ያንን ታላቅ የጦር መሪና ገናና የዓለም ገዢ የማረከው እንግሊዝ ደግሞ ጀግንነትን የማድነቅ፣ ሰብዐዊ መብትን የማክበር ባህል -ድንቅ ባህል ባለቤት ስለሆነ አክብሮ ነበር የያዘው። ናፖሊዮን ከሴንት አልባ አምልጦ እንደገና ለመቶ ቀናት ፈረንሳይን መርቷል። ማን ያውቃል የዴስቲኒን አድራሻ! ማን ያውቃል የዴስቲኒን የፍጻሜ ምዕራፍ? የዚህን ወጣት ታሪክ ከሥር መሰረቱ የሚያወጉ ወዳ ጆቹና የትግል ተካፋዮች እንዳሉ አያጠራጥርም። በመድረክና እንደኔም በመስኮቱ ንግግር ፣ ራቅ ብሎም በመሄድ የከፈለውን መስ ዋዕትነት በጨረፍታ ለምናውቀው አንድ መደምደሚያ ላይ እንደርሳለን። አንዳርጌ የሚከበር ፣ የሚወደድና በአእምሮው ትልቅነት ፣ በሰብአዊነቱና በአርቆ አሳቢነቱ – ማናቸውንም የነጻነት መስዋዕትነት ለመክፈል ባሳየው ቆራጥነቱ የሚደነቅ ነፍስ ነው። እንደሱ ያሉ ሰዎች ከጊዜያቸው በፊት መጥተው ፈተናን ሁሉ ይቀበላሉ። መንፈሱንና ስጋውን ለአምላክ እንዳስረከበ ደካማ ሰው እግዚአብ ሄርን የምለምነው አንድ ነገር አለኝ። ሲድራቅ ፣ ሚሻቅና አብድና ጎን ከሚንቀለቀለው እሳት አራት ሰው አድርጎ በፍጹም አቸናፊነ ት ያወጣቸው አምላክ ምን ይሳነዋል? በወያኔ እስር ቤት የሚንገዋለል አንበሳ በሕልሜም በውኔም ይታየኛል። እናንተስ ጎበዝ! በክ ርስቶስ ላይ ያሾፉ፣ የሾህ አክሊል በራሱ ላይ የደፉበት ፣ እስኪደክማቸው የገረፉት፣ ጎኑን የወጉት የሰው አራዊትና አራዊት ሰዎች ሥዕል አይመጣባችሁም? “ሶባጅ! ሳቬጅ!” “አኒማሌ” አል ጣልያን! ለወያኔዎች አንድ ምስጢር ልተውላቸው እወዳለሁ።

“አንዳርጋቸው ጽጌ መንፈስ ነው።”

ይህን ትንቢት ተቀበሉኝ። አምላካችን ለዚች ሀገር እንደማዕዘን ድንጋይ ሆነው ሕዝቡን የሚያገለግሉ መሪዎች ይሰጠናል። የሰራዊት ጌታ የምህረት ተስፋ ነው። እንደ ድንኳን ካስማ የሆኑ አስተዳዳሪዎችና እንደ ጦር ሜዳ ቀስት የሆኑ የጦር አዛዦችን ይሰጠናል። ብርቱ የሆኑ ጀግኖችን እንጠብቃለን። ከላይ ከጸባዖት! ከመሬቲቱ ከኢትዮጵያ ማኀጸን።እነዚህ ደግሞ የኢትዮጵያን ጠላቶች ረግጠው ከመንገድ ጭቃ ጋር እንደሚለውሱ ያደርጋል – ማን? የኃያላን ኃያል! የጌቶች ጌታ! ትዕቢተኞች ይዋረዳሉ። ዕብሪተኞች ይንኮታኮታሉ። (ከነቢዩ ኢሳያስ የትንቢት ቃል ያዳቀልሁት ነው።)

የአንዳርግ “ሌጋሲ” – ኑዛዜና ቅርስ ነው። የትውልድ ቅርስ፣ የትግል ቅርስ … የመስዋዕትነት ቅርስ! በአንዳርጋቸው ላይ የሚፈጸመውን ኢሰብዓዊ ድርጊት ሁሉ ሳስበው ከጥንት ጀምረው ኢትዮጵያን ከሰለጠነው ዓለም ጋር ለማሰለፍ ብዙ መስዋዕትነትን የከፈሉ ሰዎች እነ ሎሬንዞ ታዕዛዝ፣ ተስፋዬ ተገኝ፣ ተክለ ሃዋርያት ዋየህ፣ ሐኪም ወርቅነህ እሸቴ ቢሞቱ፤ እነ ሐዲስ ዓለማየሁ፣ ቢትወደድ ዘውዴ ገብረ ሕይወት፣ እነ አማኑኤል አብርሀም… በህይወት ቆይተው ኢትዮጵያ የገባችበትን የኋሊት ጉዞና ቅድመ መሳፍንት ዘመን አገዛዝ አይተውታል። የተጓዙበትን ርቀት ሜዳ ስለሚያስታውሱ (ለምሳሌ የባርያ አስተዳዳሪነትን ለማስቀረት የተደረገውን ያነሧል) በኢትዮጵያ አዲስ የባርያ ስርዓት የገባ ይመስላል። እንደቀድሞው በዓለም አቀፉ አካል ቁጥጥር ቢደረግ እኮ ከድርጅቱ ከሚባረሩ አገሮች ግንባር ቀደም የምትሆነው የእነ ኃይለማርያም ኢትዮጵያ በሆነች ነበር። ኢትዮጵያ ዛሬ የእነ ኃይለማርያም ናት። ነገ ነው የደቂቀ አንዳርጋቸው የምትሆነው።

አንዳርጋቸው ጽጌ በወያኔ ዓለም አቀፍ ሴራ ከተያዘበት ዕለት ጀምሮ በተለይ በውጪ ያለው ኢትዮጵያዊ በነቂስ ወጥቶ የትግል ቃል ኪዳን ሲያደርግ ይታያል። ይኽ ደግሞ የሚቀጥል ነው። ሕዝብ በራሱ አነሳሽነት ተንቀሳቅሶ በራሱ መፈክር አቋሙን ሲገልጥ ለማየት የታደልንበት አንድ አጋጣሚ የአንዳርጋቸው ሌጋሲ ይመስለኛል። “እኔ አንዳርጋቸው ጽጌ ነኝ” የሚለውን ከኢትዮጵያ ጋር የተካሄደ መሐላ በግንቦት ሰባቶች በድርጅታዊ አሰራር የመጣ መስሎ ይታይ ይሆናል። አይደለም። ሕዝቡ ጀግንነቱ፣ ወኔው፣ ወንድነቱ፣ የተሟሟቀበትና የተነሳበት ነበር ለማለት ይቻላል። በእኔ በኩል ምርኮ ተብሎ የተጠራውን “ክተት” ለማለት እወዳለሁ። …. ያገሬ ሕዝብ ጆሮ ይሰጠኝ ይሆን ?

ከጸጋዬ ገብረመድህን አረአያ ~ (ጋዜጠኛ ሙሉጌታ ሉሌ)

Filed in: Amharic